​የአሰልጣኞች አስተያየት፡ ኢትዮጵያ 2-3 ሩዋንዳ

በአፍሪካ ሃገራት ቻምፒዮንሺፕ (ቻን) ማጣሪያ የመጀመሪያ ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ ተካሂዶ ኢትዮጵያ በሩዋንዳ 3-2 ተሸንፋለች፡፡ ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ የሁለቱ ሃገራት ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኞች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

“ለተፈጠረው ነገር ህዝቤን ይቅርታ እጠይቃለሁ” የኢትዮጵያ አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ

ስለጨዋታው

“ጨዋታው መጥፎ ነው ማለት አይቻልም፡፡ ግን የተቆጠሩት ጎሎች ቅስም የሚሰብሩ ናቸው እና ህዝቤን ይቅርታ ነው የምለው፡፡ በተከታታይ ባገኘነው አጋጣሚ ጥሩ ውጤት አላመጣንም፡፡ ይህንን ህዝብ ይቅርታ ነው የምጠይቀው፡፡”

“የመጨረስ ችግር ነው፡፡ ወሳኝ አጥቂዎች ከሌሉህ ዋጋ ትከፍላለህ፡፡ ከዚህ በፊትም በዚህ ዙሪያ ላይ ብዙ ተናግሪያለው ያሉን ልጆች እንዚህ ናቸው፡፡ ከእኔ አቅም በላይ ነው እንግዲህ፡፡ ለተፈጠረው ነገር ህዝቤን ይቅርታ ነው የምጠይቅው፡፡”

ስለ ለዓለም ብርሃኑ ስህተት

“የእኔ ጥፋት ነው፡፡ ስህተቱን አምኜ እቀበላለው፡፡”

ያለቦታቸው ስለተሰለፉ ተጫዋቾች እና ቀጣይ ሁኔታ

“በኳስ ምን ሊገጥምህ አንደሚችል አታውቀውም፡፡ እንዲህ ነው ብሎ ቀድሞ መናገር ከባድ ነው፡፡ በሂደት የምናየው ነው የሚሆነው፡፡”

“አስቻለው ቦታ ላይ ፈልገን የነበረው የጅማ አባ ጅፋርን ሄኖክን ነበር፡፡ ፓስፖርት አለወጣለትም ከአርብ ጀምሮ እስከ (ቅዳሜ) ማታ ድረስ አላገኘንም፡፡ ያለን አማራጭ 10 ሰው ሆነህ አትገባም፤ ተጫዋቾችን ስንመለምል በዚህ ነበር ያሰብኩት አልተሳካም፡፡”

“ምንአልባት የተወሰኑ ልጆች ይቀላቀላሉ ብለን እናስባለን፡፡ የሚሆነው አብረን እናያለን፡፡”

“ከሜዳችን ውጪ የተሻለ ውጤት ይዘን መመለስ እንፈልግ ነበር” የሩዋንዳ አሰልጣኝ አንቶይን ሄይ

ስለጨዋታው

“በውጤቱ በጣም ደስተኛ ነን፡፡ ከሁለት ግዜ መመራት ተነስተን ነው ይህንን ያሳካነው፡፡ በመጀመሪያው አጋማሽ 1-0 እንዲሁም ከ60ኛው ደቂቃ በኃላ 2-1 መመራት ለመቀበል የሚያስቸገር ነበር፡፡ ነገር ግን ተጫዋቻችን ይህንን በሚገባ ተወጥተዋል፡፡ ይህ ያለንን የአዕምሮ ጠንካራነት ያሳያል፡፡”

“ያለን ቡድን በጣም ወጣት ነው፡፡ 20 እና 21 ዓመት የሆናቸው ተጫዋቾችን ይዘናል፡፡ ይህ ለእነሱ በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ መጫወት አዲስ አዲስ ነው፡፡ ግን በጣም ጥሩ የሆነ ነገር አሳይተዋል፡፡ እየተጫወትን ባለናቸው ግጥሚያዎችም መሻሻሎችን እያሳዩ ነው፡፡”

ስለቀጣይ ጨዋታ 

“ከእኛ የተሻለ ልምድ አላችሁ፡፡ ትንሽ ተጫዋቾቻን ላይ በአንዳንድ ሁኔታዎች የመዝናናት ነገሮችን ተመልክተናል፡፡ ገና ተጨማሪ 90 ደቂቃዎች ይቀሩናል ስለዚህ ጨዋታው አልተጠናቀቀም ገና፡፡ በእግርኳስ ሁሉም ነገር ሊፈጠር ይችላል፡፡”

ከሱዳኑ አሰልጣኝ መሃመድ ማዝዳ ጋር ያደረጉት ውይይት

“ከሱዳን አሰልጣኝ (መሃመድ ማዝዳ) ጋር ስለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አቋም ያደረጉት ንግግር ጠቅሞኛል ማለት አልችልም፡፡ አሁን ላይ የተመለከትነው ለጨዋታው የተለየ ዘዴ ይዞ የመጣ ነበር፡፡ ከሜዳችን ውጪ የተሻለ ውጤት ይዘን መመለስ እንፈልግ ነበር፡፡ ስናጠቃ ለመልሶ ማጥቃት ተጋላጭ እየሆንን ነበር ግን ጥሩ ውጤትን ይዘን ወደ ቤታችን መመለሳችን ጥሩ ነው፡፡”

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *