የብሔራዊ ቡድኑ አስገራሚ ጥያቄ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሴካፋ የመጨረሻ የምድብ ጨዋታ ነገ ዩጋንዳን ለመግጠም እየተዘጋጀች ባለበት ወቅት አስገራሚ መረጃ ከወደ ኬንያ ተሰምቷል።

በኬንያ አዘጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው የሴካፋ ዋንጫ ላይ እየተሳተፈ የሚገኘው የኢትዮዽያ ብሔራዊ ቡድን በመጀመርያ የምድብ ጨዋታው ደቡብ ሱዳንን 3-0 በሆነ ውጤት በማሸነፍ አጀማመሩን ቢያሳምርም በሴካፋ የተሳትፎ ታሪኩ ተሸንፎ በማያቀው ውጤት በቡሩንዲ 4-1 ተረትቶ ወደ ግማሽ ፍፃሜ የመግባት እድሉን አጥብቧል።

ብሔራዊ ቡድኑ ወደ ግማሽ ፍፃሜው ለማለፍ ነገ የዩጋንዳ ብሔራዊ ቡድንን የማሸነፍ ብቻ ግዴታ ውስጥ መግባቱን ተከትሎ በቡድኑ ላይ ያለው በራስ መተማመን የወረደ ይመስላል። ከኬንያ ለቡድኑ ቅርበት ካላቸው ምንጮች እንዳረጋገጥነው ከሆነ ዩጋንዳን ማሸነፍ ከባድ እንደሆነ በማሰብ የቡድኑ አባላት ሰኞ ወደ አአ የሚመጡበት የአውሮፕላን ትኬት እንዲላክላቸው ለኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ጥያቄ ጠይቀዋል። ፌዴሬሽኑም የአውሮፕላን ትኬቱን ለመላክ እንቅስቃሴ መጀመሩ ተሰምቷል።

የሴካፋ ውድድር ላይ ብሔራዊ ቡድኑ የመሳተፉ ጉዳይ ብዙ በማያሳምንበት እና ከባድ ሽንፈት ባስተናገደበት ወቅት እንዲህ ያለ መረጃ መውጣቱ አስገራሚ ሆኗል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *