በፕሪምየር ሊግ ጨዋታዎች ላይ በድጋሚ ለውጥ ተደርጓል

ነገ እና ከነገ በስትያ ሁሉም ስምንት ጨዋታዎች እንደሚስተናገዱበት ይጠበቅ የነበረው የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ለሁለተኛ ጊዜ የፕሮግራም ቅያሪ ተደርጎበታል። በቅያሪውም አንድ ጨዋታ የቀን ለውጥ ሲደረግበት ሌላኛው ደግሞ ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሟል። በዚህም መሰረት መቐለ ላይ ሊካሄድ የነበረው የመቐለ ከተማ እና መከላከያ ጨዋታ በእንግዳው ቡድን ጥያቄ መሰረት ወደ እሁድ ተሸጋግሯል። መከላከያ ጥያቄውን ያቀረበው በ26ኛው ሳምንት ጨዋታውን ያደረገው በዕለተ ማክሰኞ በመሆኑ በቂ የዝግጅት ጊዜ ለማግኘት በሚል በሚል ነው።

በሌላ በኩል ደግሞ በሀዋሳ ባለው ወቅታዊ የፀጥታ ችግር ምክንያት የሀዋሳ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና ጨዋታ ላልተወሰነ ጊዜ የተላለፈ ሲሆን ቦዲት ላይ ወላይታ ድቻ እና ወልዋሎ ዓ.ዩን እንደሚያገናኝ የሚጠበቀው ጨዋታም ሊተላለፍ የሚችልበት ዕድል ሰፊ ሆኗል። ወልዋሎ ዓ.ዩ በስፍራው ባለው የፀጥታ ሁኔታ ዙርያ ማረጋገጫ ይሰጠን በማለቱ የሊግ ኮሚቴው የጨዋታውን ቀን ለመቁረጥ የመጨረሻ ውሳኔ ላይ አልደረሰም። ኮሚቴው በጉዳዩ ዙርያ እያደረገ ያለውን ማጣራት ካገባደደ በኃላ ውሳኔውን ሲያሳውቅ ዜናውን ይዘን የምንመለስ ይሆናል።

የ27ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ መርሐ ግብር

ቅዳሜ ሰኔ 9 ቀን 2010

04:00 ፋሲል ከተማ ከ ሲዳማ ቡና (ጎንደር)

04:00 ወልዲያ ከ ጅማ አባጅፋር (አአ)

09:00 ድሬዳዋ ከተማ ከ ኤሌክትሪክ (ድሬዳዋ)

09:00 ወላይታ ድቻ ከ ወልዋሎ (ቦዲቲ)*

10:00 ደደቢት ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ (አአ)

እሁድ ሰኔ 10 ቀን 2010

09:00 መቐለ ከተማ ከ መከላከያ (መቐለ)

09:00 አዳማ ከተማ ከ አርባምንጭ ከተማ (አዳማ)

ወደሌላ ጊዜ መሸጋገሩ የተረጋገጠ

ሀዋሳ ከተማ ከ ኢትዮጵያ ቡና