በማንቸስተር ሲቲ የተፈለገው ታዳጊው ናኦል ከፌድሬሽኑ ጋር ሊወያይ ነው

የ14 ዓመቱ የወደፊት ተስፈኛ ናኦል ተስፋዬ ከኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ጋር ስለወደፊት የብሔራዊ ቡድን ምርጫው ለመወያየት ዛሬ ከተወለደባት ስዊድን ወደ አዲስ አበባ እየመጣ ይገኛል፡፡ የተጫዋቹ ቤሰተቦች ከፌደሬሽኑ ፕሬዝደንት አቶ ኢሳያስ ጂራ ጋር ውይይት እንደሚደርጉም ሰምተናል፡፡

በግራ መስመር ተከላካይነት እና የመስመር ተጨዋችነት መሰለፍ የሚችለው ናኦል ከቀድሞ የፌደሬሽኑ ፕሬዝደንት አቶ ጁንየዲ ባሻ ጋር በፈጠረው ግንኙነት ምክንያት ይህ ውይይት ሊሳካ እንደቻለ ታውቋል፡፡ “ከቀድሞ ፕሬዝደንት ወደ ኢትዮጵያ መጥቼ ሙከራ የማደረግበትን እና ከአዲሱ ፕሬዝደንት ጋር የምወያይበትን እድል አመቻችተዋል፡፡ ከቤተሰቦቼ ጋር ስለቀጣይ ሁኔታዎች ለመነጋገር ነው የምመጣው፡፡”

ናኦል በኢትዮጵያ ቆይታው ሙከራ እንደሚደርግ የሚጠበቅ ሲሆን በቅርቡ ወደ እንግሊዝ አምርቶ ፊርማውን ለአንድ ክለብ እንደሚያኖር ለሶከር ኢትዮጵያ ገልጿል፡፡ “ከወኪሎቼ ጋር በዚህ ጉዳይ ተነጋግረናል፡፡ በመጀመሪያ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ጉዳይ አጠናቅቄ ስለመለስ ከአንድ ክለብ ጋር የነበረንን ድርድር እንቀጥላለን፡፡ ከኢትዮጵያ ስለመለስ ለአንድ ክለብ እፈርማለው።” ብሏል።

የሪያል ማድሪዱ የግራ መስመር ተመላላሽ ማርሴሎ አድናቂ መሆኑን የሚናገረው ናኦል ከሲቲ በተጨማሪ ሊድስ ዩናይትድ ወደ ቡድኑ የታዳጊዎች ማሰልጠኛ ሊያስገባው ፍላጎታቸውን ካሳዩ ቡድኖች መካከል ነው።