መቐለ ከተማ ከራያ ቢራ ጋር የማልያ ስፖንሰርሺፕ ስምምነት ተፈራረመ

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የመጀመርያ ተሳትፎው 4ኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀው መቐለ ከተማ ከራያ ቢራ አ.ማ ጋር የስፖንሰርሺፕ ስምምነት መፈራረሙን አስታውቋል። 

የክለቡ ስራ አስኪያጅ አቶ ሽፈራው ተክለኃይማኖት ለሶከር ኢትዮጵያ እንደገለፁት ከቢራ አምራች ኩባንያው ጋር ለ3 ዓመት የሚቆይ የውል ስምምነት የተፈራረሙ ሲሆን 30 ሚልዮን ብር በሶስቱ ዓመታት ውስጥ ለክለቡ ገቢ ይሆናል። ከቀጣዩ የውድድር ዓመት ጀምሮም የኩባንያው ማስታወቂያ በማልያው ፊት ላይ የሚደረግ ይሆናል።

በ2007 የተቋቋመው ራያ ቢራ በኢትዮጵያ እግርኳስ ላይ የቢራ ኩባንያዎችን የስፖንሰር ልማድ ተቀላቅሏል። ከዚህ ቀደም ዳሽን ቢራ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቢራ፣ ዋልያ ቢራ፣ ሜታ ቢራ፣ ሐረር ቢራ፣ ሐበሻ ቢራ በማልያ እና በሌሎች በስፖንሰር ስምረነቶች እንዲሁም በክለብ ባለቤትነት በኢትዮጵያ እግርኳስ የተሳተፉ ናቸው።