ዋልያዎቹ ከሴራልዮን ጋር ጨዋታ የሚያደርጉበት ቀን እና ቦታ ታውቋል

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ሁለተኛ መርሐ ግብር ከሴራሊዮን ጋር የሚያደርገውን ጨዋታ የሚያካሂድበትን ቦታ እና ቀን ወስኗል። 

ካፍ የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎቹ ከጳጉሜ 2-5 ባሉት ቀናት እንደሚካሄድ አሳውቆ የነበረ ሲሆን ፌዴሬሽኑም ከሴራሊዮን የሚያደርገውን ጨዋታ እሁድ ጳጉሜ 4 ቀን 2010 በሀዋሳ ዓለምአቀፍ ስታድየም 10:00 ላይ ለማድረግ እንደወሰነ ታውቋል።

ብሔራዊ ቡድኑ በ2017 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ የመጨረሻ ጨዋታውን ሀዋሳ ላይ ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን ሲሸልስን 2-1 ማሸነፉ ይታወሳል። ስታድየሙ ከዚህ ቀደምም የሴካፋ፣ የወዳጅነት፣ የማጣርያ እና የአፍሪካ የክለብ ውድድሮችን ማስተናገዱ ይታወቃል።

ባለፈው ሳምንት አብርሀም መብራቱን አሰልጣኝ አድርጎ የቀጠረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በምድብ 5 ከጋና፣ ሴራሊዮን እና ኬንያ ጋር መደልደሉ የሚታወስ ሲሆን በመጀመርያ ጨዋታው በጋና 5-0 በመሸነፉ የምድቡን ግርጌ ይዞ ይገኛል።