የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን የዳኞች ኮሚቴ አባላት የስራ ድርሻ ድልድል ተከናወኗል

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ምርጫ ከተከናወነ በኋላ እንደ አዲስ በተዋቀረው የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ውስጥ የዳኞች ኮሜቴ ዋና ሰብሳቢ ሆነው የተሰየሙት አቶ ዮሴፍ ተስፋዬ በጳጉሜ ወር ከዳኞች ጋር በኢትዮጽያ ሆቴል ስብሰባ ማድረጋቸው የሚታወስ ነው። ባሳለፍነው ዓርብም በቀጣዩ የውድድር ዓመት የዳኞች ኮሚቴን በማወቀር በዘርፉ ለረዥም ጊዜ ያገለገሉ ስድስት ግለሰቦች በእጩነት መቅረባቸው ይታወሳል።

በዚህም መሰረት አቶ ዮሴፍ ተስፋዬ በእጩነት ይዘዋቸው ፍቃደኝነታቸው ሲጠበቅ የነበሩት ግለሰቦች ፍቃደኝነታቸውን በመግለፃቸው የ2011 የዳኞች ኮሚቴ አባላት ታውቀዋል። በዚህ መሰረትም ኢንስትራክተር ቸርነት አሰፋ ምክትል ሰብሳቢ በመሆን ሲመረጡ ኢንስትራክተር ኃይለመላክ ተሰማ የአካል ብቃት ቁጥጥር ኃላፊ በመሆን የስራ ድርሻ ተሰጥቷቸዋል። በተጨማሪም ሻለቀ በልሁ ኃይለማርያም የዳኝነት ህግ ስልጠናን የሚመለከት ኃላፊነት ሲወስዱ ኮሚሽነር ፍቃዱ ጥላሁን የአስቸኳይ ጊዜ ሰብሳቢ ፣ ኮሚሽነር ሲያምረኝ ዳኜ እና ኮሚሽነር አበጋዝ ነብየልዑል በኮሚቴው ውስጥ አባል በመሆን የሚሰሩ ይሆናል።

የተመረጡት ግለሰቦች በ2011 የዳኞችን ኮሜቴ ውስጥ የተሰጣቸውን የስራ ድርሻ በሚመለከት እና በመጪው የውድድር ዓመት እቅድ ዙርያ ነገ (ሰኞ) ሰፋ ያለ የስብሰባ ለማድረግ ፕሮግራም መያዙ ታውቋል።