የፌደራል ፖሊስ ይግባኝ ውድቅ ተደርጓል

ነሀሴ 14 ቀን 2010 ፌደራል ፖሊስ ከሽረ እንዳሥላሴ ባደረጉት የ30ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የምድብ ሀ ጨዋታ ባለሜዳዎቹ ፌደራል ፖሊሶች ያቀረቡት የተጨዋች ተገቢነት ክስ አስመልክቶ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የከፍተኛ ሊግ ኮሚቴ ጉዳዩን መርምሮ አራት ገፆች እባሪ በማድረግ ጳግሜ 1 ውሳኔውን ለክለቦቹ ማሳወቁ ይታወሳል።

ፌደራል ፖሊስ ስፖርት ክለብ በሽረ እንዳስላሴ ተጨዋቾች ልደቱ ለማ እና ሰኢድ ሁሴን ላይ ባቀረበው ክስ የፌደሬሽኑ የከፍተኛ ሊግ ኮሚቴ ጳግሜ 1 በላከው ደብዳቤ ክሱን ውድቅ ማድረጉን እና ክለቡ ወደ 3ኛው የኢትዮጵያ የሊግ እርከን (የኢትዮጵያ አንደኛ ሊግ) የወረደው በአግባቡ ህግ እንደሆነ በመግለው ውሳኔውን ማሳወቁ ይታወቃል። ፖሊሶች ግን ይህንን ውሳኔ በመቃወም ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ይግባኝ ሰሚ ኮሚቴ ይግባኝ በማለት የኮሚቴውን ውሳኔ ሲጠብቁ ቆይተው ኮሚቴውም ከቀናት በፊት ባወጣው የውሳኔ ደብዳቤ ቀድሞ የፌደሬሽኑ የዲሲፕሊን ኮሚቴ ያስተላለፈው ውሳኔ እንዲፀና እና ይግባኝ ባይ (ፌደራል ፖሊስ) ያቀረበው የይግባኝ አቤቱታ በአብዛኛው ክፍል የፀና በመሆኑ ለፌደሬሽኑ ያስያዘው የይግባኝ ማስከፈቻ 150,000 ( አንድ መቶ ሀምሳ ሺ ብር) ለፌደሬሽኑ ገቢ እንዲሆን ወስኗል።