መቐለ ከተማ የስያሜ ለውጥ አደረገ

መቐለ ከተማ እግር ኳስ ክለብ የሚታወቅበትን ስያሜ በመተው “መቐለ 70 እንደርታ እግርኳስ ክለብ” ወደሚል አዲስ ስያሜ መቀየሩ ታውቋል። 

ከባለፈው የውድድር ዓመት ጀምሮ የስያሜ እና የሎጎ ቅያሪ ለማድረግ በደጋፊ ማህበሩ አማካኝነት ደጋፊዎችን ያሳተፈ ምርጫ ሲያካሂድ የቆየው ክለቡ በመጨረሻ ላይ ስያሜውን ወደ መቐለ 70 እንደርታ ሲቀይር የሎጎ ለውጥ ለማረግ ጥናት እየደረገ መሆኑ ከክለቡ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

በ1950ዎቹ መጀመርያ እንደተመሰረተ የሚነገርለት ይህ ክለብ በ እነ ኃይለ  ኃ/መስቀል ፣ ገ/መስቀል ዓባይ እና ሌሎች ግለሰቦች አማካኝነት ሲመሰረት እንደርታ በሚል ስያሜ የነበረው ሲሆን ብዙም ሳይቆይ በራሕለይ በሚል ስያሜ ተቀይሯል። ከዛ በኋላም በተለያዩ ምክንያቶች ስያሜ ሲቀያይር ከቆየ በኋላ በ2002 እስካሁን ሲጠቀምበት የነበረውን እና በ1980ዎቹም ሲጠቀምበት የነበረው መቐለ ከተማን መጠሪያው አድርጎ እስከ ዘንድሮ ቆይቶ ነበር።