ሀዋሳ ከተማ መሐመድ ናስርን አስፈርሟል

የአጥቂ ስፍራ ተጫዋች ሲያፈላልግ የነበረው ሀዋሳ ከተማ መሐመድ ናስርን ወደ ክለቡ አምጥቷል፡፡ አንጋፋው አጥቂ በ2011 የውድድር ዘመን መጀመር በ2 ዓመት ውል ፋሰል ከነማ ተቀላቅሎ የነበረ ቢሆንም ቀሪ የአንድ ዓመት ውል እያለው በስምምነት በመለያት ወደ ሀዋሳ ከተማ በአንድ ዓመት የውል ስምምነት አምርቷል፡፡

በ1990ዎቹ መጨረሻ ለጅማ ከተማ (አባ ጅፋር) በመጫወት ወደ ኢትዮጵያ እግርኳስ ብቅ ያለው መሐመድ ኒያላ፣ መከላከያ፣ ኤሌክትሪክ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮጵያ ቡና፣ አዳማ ከተማ፣ አል-አህሊ ሸንዲ፣ ኢትዮጵያ መድን፣ ጅማ አባ ቡና እና ፋሲል ከነማ ሌሎች ተጫውቶ ያሳለፈባቸው ክለቦች ናቸው፡፡

ሀዋሳ ከተማ ዝውወሩን ተከትሎ በአጥቂ ስፍራ ላይ የወጣቶች እና የአንጋፎች ስብጥርን መያዝ ችሏል፡፡ እስራኤል እሸቱ እና ገብረመስቀል ዱባለ የወደፊት ተስፋዎች ሲሆኑ አዲስ ፈራሚዎቹ አዳነ ግርማ እና መሐመድ ናስር ለረጅም ዓመታት በሊጉ የተጫወቱ አጥቂዎች ናቸው፡፡