ስሑል ሽረ የማልያ ስፖንሰር ተፈራርሟል

አዲስ አዳጊው ስሑል ሽረ ከራያ ቢራ ጋር የማልያ ስፖንሰር የተፈራረመ ሦስተኛው የትግራይ ክለብ ሆኗል።

ከከፍተኛ ሊጉ በሦስተኝነት አድጎ ትናንት በመጀመሪያ የፕሪምየር ሊግ ጨዋታው ከወላይታ ድቻ ጋር ነጥብ የተጋራው ስሑል ሽረ የማልያ ስፖንሰር አግኝቷል። ከሽረ እንደስላሴ ወደ ስሑል ሽረ የስያሜ ለውጥ ማድረጉ የሚታወሰው ክለቡ የመለያ ስፖንሰር ስምምነቱን የተፈራረመው ከራያ ቢራ ጋር ነው። የሁለቱ ተቋሞች ስምምነት ለሦስት ዓመታት የሚዘልቅ ሲሆን የ30 ሚሊየን ብር ዋጋ እንዳለውም ታውቋል።

ከዚህ በፊት ከሌሎቹን የትግራይ ክለቦች መቐለ 70 እንደርታ እና ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር ተመሳሳይ ስምምነቶች የፈፀመው ራያ ቢራ አሁን ደግሞ ከሦስተኛው የክልሉ ክለብ ጋር አብሮ ለመስራት ተስማምቷል። ራያ ቢራ ከ30 ሚሊዮን ብሩ በተጨማሪ ደግሞ ሃምሳ ሺህ የደጋፊ ማልያዎችን ለማሰራት እና ከአንድ ሳጥን ሽያጭ ላይ ሁለት ብር ለክለቡ አንድ ብር ደግሞ ለደጋፊ ማህበሩ ለማበርከትም ተስማምቷል።