ቻምፒየንስ ሊግ | ጅማ አባጅፋር 18 ተጫዋቾችን  በመያዝ ዛሬ ወደ ካይሮ ይጓዛል

ቶታል ካፍ ቻምፒየንስ ሊግ የመጀመርያውን ቅድመ ማጣሪያ የጅቡቲውን ቴሌኮም በድምር ውጤት 5 – 3 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር ያለፈው ጅማ አባ ጅፋር የግብፁ ኃያል ክለብ አል አህሊን ለመግጠም ዛሬ እኩለ ለሊት ላይ 18 ተጫዋቾችን በመያዝ ወደ ካይሮ ያቀናል።   

ጅማ አባጅፋር ሁለተኛውን የሊጉን ጨዋታ ከሜዳቸው ውጭ ባሳለፍነው እሁድ ከስሑል ሽረ ጋር ያለ ጎል በአቻ ውጤት ከተለያየ በኋላ ሰኞን በማረፍ ትላንት ማምሻውን በሚገኙበት ሆቴል በጂም ልምዳቸውን ሰርተዋል። ዛሬ ወደ ካይሮ ከማቅናታቸው በፊት ፍላሚጎ አካባቢ በሚገኘው  35 ሜዳ የመጨረሻ ልምምዳቸውን ሲሰሩ  25 ተጫዋች የተገኙ ሲሆን በቴሌኮም የመልስ ጨዋታ ላይ በጉዳት ምክንያት ከጨዋታው ውጭ የነበሩት ግብጠባቂው ዘሪሁን ታደለ እና ዐወት ገ/ሚካኤል ለጨዋታው ዝግጁ ሲሆኑ የተቀሩት ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት ላይ ይገኛሉ።

አርብ ማምሻውን 02:00 ላይ ቢደረገው  ጨዋታ ጅማ አባጅፋሮች ጠንካር ያለ ፈተና እንደሚጠብቃቸው ሲገመት አሰልጣኝ ዘማርያም ወ/ጊዮርጊስም በመጀመርያው ቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ላይ ያልተጠቀሙባቸው አማካዩ አክሊሉ ዋለልኝ እና አጥቂውን ቢስማርክ አፒያን በአሁኑ ጨዋታ ቡድናቸው ውስጥ በማካተት በድምሩ 18 ተጫዋቾችን በመያዝ ዛሬ እኩ ለሊት ላይ ወደ ግብፅ ይጓዛሉ። 

ወደ ካይሮ የሚያቀኑት 18 ተጫዋቾች ስም ዝርዝር

ግብ ጠባቂዎች፡ ዳንኤል አጄይ፣ ዘሪሁን ታደለ

ተከላካዮች: አዳማ ሲሶኮ ፣ ኤልያስ አታሮ ፣ ተስፍዬ መላኩ ፣ ያሬድ ዘውድነህ ፣ ከድር ኸይረዲን፣ ዐወት ገ/ሚካኤል

አማካዮች፡ አክሊሉ ዋለልኝ ፣ መስዑድ መሐመድ ፣ ኤልያስ ማሞ ፣ ይሁን እንደሻው ፣ ኄኖክ ገምቴሳ ኤርሚያስ ኃይሉ ፣ አስቻለው ግርማ

አጥቂዎች፡ ዲዲዬ ለብሪ ፣ ሴዲቤ ማማዱ ፣ ቢስማርክ አፒያ