ሴቶች 1ኛ ዲቪዝዮን | ጌዴኦ ዲላ ከሜዳው ውጪ አሸንፏል

የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አንደኛ ዲቪዝዮን ስምንተኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ በተካሄደ ጨዋታ ሲጠናቀቅ ጌዴኦ ዲላ አአ ከተማን አሸንፏል።

አስቀድሞ እሁድ ሊካሄድ መርሐ ግብር ወጥቶለት በአፍሪካ ውድድር ምክንያት ወደ ዛሬ 10:00 የተሸጋገረው የአዲስ አበባ ከተማ እና ጌዴኦ ዲላ ጨዋታ በአዲስ አበባ ስታድየም ተካሂዶ በዲላ 1-0 አሸናፊነት ተጠናቋል። ተመጣጣኝ እና በሙከራዎች ያልታጀበ ቀዝቃዛ እንቅስቃሴ በታየበት ጨዋታ የግብ እድል በመፍጠር ቅድሚያ የያዙት እንግዶቹ ነበሩ። በ3ኛው ደቂቃ በተከላካዮች መሐል የተሻገረውን ኳስ ረድዔት አስረሳኸኝ በጠረሩ ሁኔታ ተቆጣጥራ ወደ ግብ ብትልከውም የአዲስ አበባዋ ግብ ጠባቂ ሳሳሁልሽ ሥዩም አድናባታለች። በኳስ ቁጥጥር የተሻሉ የነበሩት አአ ከተማዎች እንቅስቃሴያቸው ከተጋጣሚ የግብ ክልል የራቀ በመሆኑ የጎል እድል ለመፍጠር ሲቸገሩ ተስተውሏል። በ22ኛው ደቂቃ ከመሐል ሜዳ የተሻገረውኝ ሰንጣቂ ኳስ ከተከላካዮች አምልጣ የተቆጣጠረችው ሔለን መለሰ ከግብ ጠባቂዋ አንድ ለአንድ ተገናኝታ በመሞከር የግቡ አግዳሚ የመለሰበት ሙከራም በመጀመርያው አጋማሽ በአዲስ አበባ በኩል የታየ ብቸኛ የጎል ሙከራ ነበር።

ከተጋጣሚያቸው በተሻለ ወደ አደጋ ክልል ሲደርሱ የነበሩት ጌዴኦ ዲላዎች በ31ኛው ደቂቃ የጨዋታውን ብቸኛ ጎል አግኝተዋል። ከመስመር የተሻገረውን ኳስ ረድዔት ሞክራ ሳሳሁልሽ ብታድነውም በቅርብ ርቀት የነበረችው ትንቢት ሣሙኤል አስቆጥራለች።

ሁለተኛው አጋማሽ እጅግ የተቀዛቀዘ እንቅስቃሴ የታየተበት ሲሆን አዲስ አበባዎች የአቻነት ጎል ፍለጋ ቢንቀሳቀሱም በጌዴኦ ዲላ ተጫዋቾች በቀላሉ በቁጥጥር ስር ሲውል ተስተውሏል። በ48ኛው ደቂቃ ፎዚያ መሐመድ ያገኘችውን ጥሩ እድል ወደ ግብ መትታ ወደ ውጪ ከወጣባት ሙከራ ውጪም ተጨማሪ አጋመየጣሚ ሳይፈጥሩ ጨዋታው በጌዴኦ ዲላ 1-0 አሸናፊነት ተጠናቋል።

8ኛ ሳምንት
ቅዳሜ ጥር 4 ቀን 2011
ኢትዮ ኤሌክትሪክ 0-3 ቅዱስ ጊዮርጊስ
እሁድ ጥር 5 ቀን 2011
መከላከያ 2-0 ጥረት ኮርፖሬት
ሀዋሳ ከተማ 2-0 ድሬዳዋ ከተማ
ጥሩነሽ ዲባባ 0-1 ኢትዮ ንግድ ባንክ
አዳማ ከተማ 3-1 አርባምንጭ ከተማ
ሰኞ ጥር 6 ቀን 2011
አዲስ አበባ ከተማ 0-1 ጌዴኦ ዲላ
_____

9ኛ ሳምንት
እሁድ ጥር 12 ቀን 2011
ኢትዮ ንግድ ባንክ 08:00 አዳማ ከተማ
ጥረት ኮርፖሬት 09:00 ጥሩነሽ ዲባባ
አርባምንጭ ከተማ 09:00 ሀዋሳ ከተማ
ድሬዳዋ ከተማ 09:00 አዲስ አበባ ከተማ
ጌዴኦ ዲላ 09:00 ኢትዮ ኤሌክትሪክ
ቅዱስ ጊዮርጊስ 10:00 መከላከያ
_____

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *