ወልዋሎ የአሰልጣኙን ውል አራዘመ

አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ከወልዋሎ ዓ/ዩ ጋር እንደሚቀጥሉ ተረጋግጧል።

ከትናንት በስቲያ ወልዋሎዎች ከዋና አሰልጣኛቸው ዮሃንስ ሳህሌ ጋር ለመቀጠል መስማማታቸው መግለፃችን ይታወሳል። ትናንት ደግሞ ክለቡ ከአሰልጣኙ ጋር በይፋ በመፈራረሙ አሰልጣኙ እስከ ቀጣዩ የውድድር ዓመት መጨረሻ ድረስ ከቡድኑ ጋር እንደሚቆዩ ተረጋግጧል። በጥር ወር ቡድኑን ተረክበው የስድስት ወራት ቆይታ ያደረጉት አሰልጣኙ ከወዲሁ ለቀጣይ ዓመት ስራዎችን መጀመራቸው ሲታወቅ ከዛሬ ጀምሮ ተጫዋቾች ለማስፈረም እንቅስቃሴዎች እንደሚጀምሩ ይጠበቃል።

ባለፉት ዓመታት በፕሪምየር ሊጉ ደደቢት ፣ መቐለ 70 እንደርታ እና ድሬዳዋ ከተማን ማሰልጠን የቻሉት አሰልጣኝ ዮሐንስ በተጠናቀቀው የውድድር ዓመት ከወልዋሎ ጋር በነበታቸው ቆይታ ለአዲስ አዳጊዎቹ ሠመረ ሃፍታይ ፣ ስምዖን ማሩ እና ሽሻይ መዝገቦ የመጫወት ዕድል በመስጠታቸው ከደጋፊው ተቀባይነት ማግኘታቸው ይታወሳል።


© ሶከር ኢትዮጵያ

በድረ-ገጻችን ላይ የሚወጡ ጽሁፎች ምንጭ ካልተጠቀሱ በቀር የሶከር ኢትዮጵያ ናቸው፡፡ እባክዎ መረጃዎቻችንን በሚጠቀሙበት ወቅት ምንጭ መጥቀስዎን አይዘንጉ፡፡