ትግራይ ስታዲየም የመጀመሪያ የብሔራዊ ቡድን ጨዋታን ያስተናግዳል

በካፍ እውቅና ሳያገኝ በመቆየቱ እስካሁን የብሄራዊ ቡድን ጨዋታ ያላስተናገደው የትግራይ ስታዲየም የመጀመሪያ ጨዋታውን እንዲያስተናግድ መወሰኑን የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።

በካሜሩን አስተናጋጅነት በሚካሄደው የ2020 የአፍሪካ ሃገራት ሻምፒዮና (ቻን) ለመሳተፍ የማጣሪያ ጨዋታዋን እያደረገች የምትገኘው ኢትዮጵያ ሁለተኛ የማጣሪያ ጨዋታዋን ከሩዋንዳ ጋር ታደርጋለች። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽንም መሰከረም 11 ቀን 2012 የሚደረገውን የመጀመርያ ጨዋታ በትግራይ ስታዲየም እንዲከናወን መወሰኑን አስታውቋል።

የፊታችን እሁድ (ነሃሴ 19) በመቐለ 70 እንድርታ እና ካኖ ስፖርት መካከል የሚደረገውን የካፍ ቻምፒዮንስ ሊግ የመልስ ጨዋታ በማስተናገድ የመጀመሪያ አህጉራዊ ጨዋታ የሚያስተናግደው ስታዲየሙ ከአንድ ወር በኋላ ሁለተኛ አህጉራዊ ጨዋታ ይካሄድበታል።

የትግራይ እና የባህር ዳር ስታዲየሞች በጊዜያዊነት ውድድሮችን እንዲያስተናግዱ በካፍ መወሰኑ ይታወሳል።


© ሶከር ኢትዮጵያ

በድረ-ገጻችን ላይ የሚወጡ ጽሁፎች ምንጭ ካልተጠቀሱ በቀር የሶከር ኢትዮጵያ ናቸው፡፡ እባክዎ መረጃዎቻችንን በሚጠቀሙበት ወቅት ምንጭ መጥቀስዎን አይዘንጉ፡፡