ሎዛ አበራ ለማልታው ክለብ ፊርማዋን አኖረች

ሎዛ አበራ ለማልታው ቻምፒዮን ቢርኪርካራ በአንድ ዓመት የውል ስምምነት ዛሬ መፈረሟ ተረጋግጧል፡፡

ባለፈው የውድድር ዓመት አጋማሽ በስዊድኑ ከንግስባካ የሙከራ ጊዜን አሳልፋ በአንዳንድ ጉዳዮች ባለመስማማቷ በሁለተኛው ዙር ወደ ኢትዮጵያ ተመልሳ ለአዳማ ከተማ በመፈርም የፕሪምየር ሊግ አሸናፊ የሆነችው ሎዛ አበራ ወደ ማልታ አምርታ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን ያለፉትን ሦስት ዓመታት በተከታታይ የማልታ ሊግ አሸናፊ በሆነው ቢርኪርካራ የሙከራ ጊዜን ለጥቂት ቀናት ካሳለፈች በኋላ መፈረሟን ወኪሏ ሳምሶን ናስሮ ለሶከር ኢትዮጵያ ገልጿል፡፡

የክለብ እግር ኳስ ህይወቷን በሀዋሳ ከተማ የጀመረችሁ ሎዛ በ2007 ወደ ደደቢት ካመራች በኋላ ራሷን ከፍ ያለ ደረጃ ላይ ማድረስ የቻለች ሲሆን ለተከታታይ 4 ዓመታትም የሊጉ ኮከብ ጎል አስቆጣሪ ሆና ማጠናቀቅ ችላለች። በቱርኩ አንታናይስፖር እና በስዊድኑ ከንግስባካ ከዚህ ቀደም የሙከራ ጊዜ ያሳለፈችው ሎዛ በቱርክ ከምትገኘው ግብ ጠባቂዋ ዳግማዊት መኮንን በመቀጠል ለአውሮፓ ክለብ የፈረመች ሁለተኛ ኢትዮጵያዊትም ሆናለች፡፡


© ሶከር ኢትዮጵያ