ስሑል ሽረ ሁለት ተጫዋቾች ለማስፈረም ተስማማ

ስሑል ሽረዎች ብሩክ ሐድሽ እና ኃይለአብ ኃይለሥላሴን ለማስፈረም ከስምምነት ደርሰዋል።

የእግርኳስ ህይወቱን በትራንስ ሁለተኛ ቡድን የጀመረው አማካዩ ኃይለአብ በዋና ቡድን ደረጃ ለመቐለ 70 እንደርታ መጫወት ጀምሮ በ2005 ለደደቢት ቢፈርምም ከቡድኑ ጋር ረጅም ቆይታ ሳያደርግ ነበር ለወልዋሎ እና መቐለ በድጋሚ መጫወት የቻለው። ባለፈው ዓመት መጀመርያ ከጉዳት መልስ በመቐለ ያለፈውን የውድድር ዓመት ከምዓም አናብስት ጋር ቆይታ ያደረገው አማካዩ ለስሑል ሽረ አማካይ ክፍል ጥሩ አማራጭ ይፈጥራል ተብሎ ይገመታል።

ሌላው ለስሑል ሽረ ለመጫወት የተስማማው አጥቂው ብሩክ ሐድሽ ነው። ላለፉት ወራት ከቡድኑ ጋር ልምምድ በማድረግ የቆየው አጥቂው ባለፈው ዓመት ሰበታ ከተማ ወደ ፕሪምየር ሊጉ ሲያድግ የቡድኑ አባል እንደነበር የሚታወስ ሲሆን ከሁለት ዓመት ቆይታ በኋላ ወደ ቀድሞ ክለቡ የሚመለስ ይሆናል። ከዚ በፊት በስሑል ሽረ ፣ ትግራይ ውሃ ስራዎች እና ሰበታ ከተማ መጫወት የቻለው ይህ ተጫዋች በፊት አጥቂነት እና በመስመር መጫወት የሚችል ተጫዋች ነው።


© ሶከር ኢትዮጵያ