የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሦስተኛ ሳምንት ቁጥሮች እና እውነታዎች

የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሦስተኛ ሳምንት በሳምንቱ መጨረሻ መካሄዳቸው ይታወሳል። ሶከር ኢትዮጵያም እንደተለመደው በሳምንቱ ዙርያ ያሉትን መረጃዎች በቁጥሮች እና እውነታዎች ታገባድዳለች።

ጎል

– በሦስተኛ ሳምንት በአጠቃላይ 11 ጎሎች ተቆጥረዋል። ይህም ባለፈው ሳምንት ከተቆጠረው በግማሽ ያነሰ ነው።

– በስድስት ጨዋቻዎች ጎል ሲቆጠሩ በቀሪዎቹ ሁለት ጨዋታዎች ደግሞ ጎሎች አልተቆጠሩም።

– የዚህ ሳምንት 11 ጎሎች በ10 የተለያዩ ተጫዋቾች ሲቆጠር የወልዋሎው ጁኒያስ ናንጂቡ ሁለት ጎሎች በማስቆጠር ብቸኛው ነው።

– ለተቆጠሩት 11 ጎሎች 9 ተጫዋቾች አመቻችተው በማቀበል ተሳትፈዋል። የሲዳማ ቡናው ሀብታሙ ገዛኸኝ ደግሞ ሁለት ኳስ በማመቻቸት ቀዳሚው ነው።

– ከተቆጠሩት 11 ጎሎች መካከል 8 በእግር፣ 3 በግንባር ተገጭተው ተቆጥረዋል። ሁሉም ጎሎች የተቆጠሩትም በተጋጣሚ ሳጥን ውስጥ ተመትተው ነው። ሦስት ጎሎች ደግሞ መነሻቸውን ከቆመ ኳስ አድርገዋል።

– ጎል አስቆጣሪዎችን በጨዋታው የሰለፉበትን ቦታ ስንመለከት 7 ጎሎች በስድስት አጥቂዎች ሲቆጠሩ፤ 3 ጎሎች በመስመር ተጫዋቾች ተቆጥረዋል። ቀሪዋ አንድ ጎል ከተከላካይ አማካይ የተገኘች ነበረች።

– አዳማ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በዚህ ሳምንትም ጎል ሳይቆጠርባቸው ወጥተዋል። እስካሁን በሊጉ ጎል ያልተቆጠረበቸው ቡድኖችም ናቸው።

– በሦስት ሳምንታት ሁሉሕ የሊግ ቡድኖች ጎል አስቆጥረዋል።

የመጀመርያዎቹ

– ፋሲል ከነማን 1-0 ያሸነፈው ወልቂጤ ከተማ በታሪኩ የመጀመርያ ድል እና ጎል ማሳካት ችሏል።

– ወልቂጤ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና ዓመቱ የመጀመርያ ጎላቸውን አግኝተዋል።

– ድሬዳዋ ከተማ እና ወልቂጤ የዓመቱ የመጀመርያ ድላቸውን አሳክተዋል።

– ከአዳማ ጋር ነጥብ የተጋራው ሰበታ ከተማ የዓመቱን የመጀመርያ ነጥብ አሳክቷል።

– የወልቂጤ ከተማው ኤፍሬም ዘካርያስ በሁለት ቢጫ ከሜዳ የወጣ የዓመቱ የመጀመርያ ተጫዋች ሆኗል። (ከዚህ ቀደም በቀጥታ ቀይ ሁለት ተጫዋቾች ወጥተዋል)

ካርዶች

– በ3ኛው ሳምንት በአጠቃላይ 19 የማስጠንቀቂያ ካርድ እና 1 ቀይ ካርድ (በሁለት ቢጫ) ተመዟል። ይህም ካለፈው ሳምንት ጋር ሲነፃፀር በ15 ካርዶች ዝቅ ብሏል።

– ወልቂጤ ከ ፋሲል ባደረጉት ጨዋታ ቀይ ካርድ የተመለከተው ኤፍሬም ዘካርያስ በውድድር ዓመቱ ሦስተኛ ከሜዳ የተወገደ ተጫዋች ሆኖ ሲመዘገብ በሁለት ቢጫ በመሰናበት የመጀመርያው ነው።

– ወልቂጤ ከ ፋሲል ያረጉት ጨዋታ በርካታ ካርድ የተመዘዘበት ሆኖ ተመዝግቧል። (3 ቢጫ እና አንድ ቀይ)

– በዚህ ሳምንት ምንም ካርድ ያልተመዘዘበት ጨዋታ በወላይታ ድቻ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ መካከል የተደረገው ነው።

– እስካሁን በፕሪምየር ሊጉ በአጠቃላይ በ24 ጨዋታዎች 66 ቢጫ እና ሦስት ቀይ ካርድ ተመዝግቧል።


© ሶከር ኢትዮጵያ