የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች የሴቶች ብሔራዊ ቡድን ልምምዱን እየሰራ ይገኛል

በህንድ አስተናጋጅነት ለሚካሄደው ከ17 ዓመት በታች የሴቶች ዓለም ዋንጫ የማጣሪያ ጨዋታ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች የሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዝግጅቱን ከጀመረ ቀናት አስቆጥሯል።

አሰልጣኝ ሳሙኤል አበራ እና ሰርካዲስ እውነቱ የሚመራው ቡድኑ ከዩጋንዳ ጋር ላለበት የመጀመርያ የማጣርያ ጨዋታ ባሳለፍነው ሳምንት ለ24 ተጫዋቾች ጥሪ ማድረጋቸው ይታወቃል።

ሆኖም ለ24 ተጫዋቾች አስቀድመው ጥሪ ያደረገ ቢሆንም ምክንያቱ ለጊዜው ባልታወቀ ሁኔታ ተጨማሪ 16 ተጫዋቾችን ከተለያዩ ክለቦች ጥሪ በማድረግ በድምሩ 40 ተጫዋቾችን በመያዝ ለአራት ቀናት ምልመላ ሲያደርጉ ቆይቷል።

በመጀመርያው ዙር ጥሪ ከተደረገላቸው ተጫዋቾች መካከል ግብጠባቂ ዓባይነሽ ሄርቄሎ፣ ፀሐይነሽ በቀለ፣ ሜላት አልሙዝ፣ ትዕግስት ወርቁ እና ፀጋነሽ ወለና በመቀነስ በምትካቸው ትዕግት ኃይሌ (ከኤሌክትሪክ)፣ ጽዮን ፈለቀ (ከቅዱስ ጊዮርጊስ)፣ ጥሩወርቅ ወዳጁ (ከባህር ዳር ከተማ)፣ እና እሌኒ አበበ (ከቅዱስ ጊዮርጊስ) በመምረጥ የመጨረሻ 23 ተጫዋቾችን በመያዝ ከትናትናው ምሽት ጀምሮ ዝግጅታቸውን በአዲስ አበባ ስታድየም ጀምረዋል።

ለቀናት በአዲስ አበባ ስታድየም ልምምዳቸውን ሲሰሩ ቆይተው 20 ተጫዋቾችን በመያዝ የመጀመርያ የማጣርያ ጨዋታቸውን ጥር 2 ቀን ካምፓላ ላይ የዩጋንዳ አቻቸውን የሚገጥሙ ይሆናል።

ከጉዟቸው አስቀድሞ የቡድኑ አሰልጣኝ እና አምበል በብሔራዊ ቡድኑ ወቅታዊ አቋም ዙርያ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ የሚሰጡ ተብሎ ይጠበቃል።


በአዲስ መልክ የተመረጡ ተጨዋቾች ዝርዝር

ግብ ጠባቂዎች

ፎዚያ ዝናቡ፣ ባንቺአየሁ ደምመላሽ፣ ዓይናለም ሽታ

ተከላካዮች

ትዕግስት ኃይሉ፣ ፀሀይነሽ በቀለ፣ ሀና ኃይሉ፣ ነፃነት ፀጋዬ፣ የምስራች ሞገስ፣ ጥሩወርቅ ወዳጁ፣ ቤቲ በቀለ፣ ቃልኪዳን ተስፋዬ

አማካዮች

ይመችሽ ዘመዴ፣ ማዕድን ሳህሉ፣ ፋሲካ መስፍን፣ መሳይ ተመስገን፣ እሌኒ አበበ፣ ኝቦኝ የን፣ ዮርዳኖስ በርኸ፣ መዲና ጀማል

አጥቂዎች

ፋና ዘነበ፣ ንግስት በቀለ ፣ አርያት ሁዶንግ፣ ሠርክዓለም ባሳ

© ሶከር ኢትዮጵያ