ከሸገር ደርቢ ከ1 ሚልዮን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ተጠባቂው የሸገር ደርቢ ዛሬ ሲካሄድ በአዲስ አበባ ስታዲየም የተገኘው ተመልካች ቁጥር እና የገቢ መጠን ታውቋል።

10፡00 ላይ የተደረገውና በቅዱስ ጊዮርጊስ 1-0 አሸናፊነት የተጠናቀቀውን ጨዋታ በክቡር ትሪቡን የገቡትን ተመልካቾች እና ሌሎች አካላት ሳይጨምር 24,448 ተመልካች መግባቱን ለማወቅ ችለናል። ከዚህ የተመልካች ቁጥርም 1,236,480 ብር ገቢ ተገኝቷል። የትሪቡኑ ገቢ ሲጨመርም ገቢው ከዚህ ሊልቅ እንደሚችል ይገመታል።

ሁለቱ ክለቦች ከልማዳዊ የትኬት አሻሻጥ በመውጣት ከዳሸን ባንክ አሞሌ ጋር ስምምነት በመፍጠር ከስታዲየም በሮች ውጪ የመግቢያ ትኬቶች መሸጥ መጀመራቸው የሚታወስ ሲሆን የክፍያ መጠኑ መጨመር ባለፉት ሳምንታት መነጋገርያ ቢሆንም ዛሬ የገባው ገቢ መጠን በአዲስ አበባ ስታዲየም ከተገኙት ገቢዎች ሁሉ የላቀው እንደሆነ ይታመናል።

በዛሬው ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ቅዱስ ጊዮርጊስ አስቀድመው ባደረጉት ስምምነት መሠረት በሁለት የደርሶ መልስ ጨዋታ የሚገኘውን ገቢ እኩል ለመካፈል መስማማታቸው ይታወሳል።

© ሶከር ኢትዮጵያ