ስሑል ሽረ ከመስመር ተከላካዩ ጋር በስምምነት ተለያየ

ባለፈው የውድድር ዓመት ስሑል ሽረን ተቀላቅሎ ከቡድኑ ጋር የአንድ ዓመት ከስድስት ወር ቆይታ ያደረገው የመስመር ተከላካዩ ዓብዱሰላም አማን ከቡድኑ ጋር በስምምነት ተለያይቷል።

ለደደቢት ፣ ዳሽን ቢራ ፣ ኢትዮጵያ ቡናና ወልዋሎ መጫወት የቻለው ይህ የመስመር ተከላካይ ባለፈው የውድድር ዓመት ቡድኑ በፕሪምየር ሊጉ እንዲቆይ ትልቅ ድርሻ እንደነበረው የሚታወስ ሲሆን በዘንድሮ የውድድር ዓመትም በጥቂት ጨዋታዎች ተሰልፎ ቡድኑን አገልግሏል። ከደደቢት ታዳጊ ቡድን የተገኘው ይህ ተጫዋች በ2009 የወልዋሎ ቆይታውም ቡድኑ ወደ ፕሪምየር ሊጉ ሲያልፍም ትልቅ ድርሻ እንደነበረው ይታወሳል።

ሲሳይ አብርሀም አዲስ አሰልጣኝ አድርገው የቀጠሩት እና ሦስት ዝውውሮች የፈፀሙት ስሑል ሽረዎች በቀጣይ ቀናት አዳዲስ ተጫዋቾች ያስፈርማሉ ተብሎ ይጠበቃል።

© ሶከር ኢትዮጵያ