ወልቂጤ ከተማ አንድ ተጫዋች ሲያስፈርም የነባሩን ውል አድሷል

ፍሬው ሰለሞን ወልቂጤ ከተማን ለመቀላቀል ሲስማማ አሳሪ አልመሐዲ ውሉን አድሷል።

የነባር ተጫዋቾችን ውል ከሰሞኑ ሲያራዝሙ የነበሩት እና አራት ተጫዋቾችን አስፈርመው የነበሩት ወልቂጤ ከተማዎች የአማካይ ስፍራ ተጫዋች ፍሬው ሰለሞን በሁለት ዓመት ውል ወደ ክለባቸው በመቀላቀል የአዳዲስ ተጫዋቾችን ቁጥር አምስት አድርሰዋል፡፡ የቀድሞው የሀላባ ከተማ፣ ሙገር ሲሚንቶ እና ሀዋሳ ከተማ ተጫዋች ሀዋሳ ከተማን በ2010 ከለቀቀ በኃላ በድጋሚ ወደ ቀድሞው ክለቡ መከላከያ ተመልሶ ሁለት ዓመታትን መቆየት ችሏል፡፡ ይህ የአማካይ ስፍራ ተጫዋች ከሰሞኑ ወደ ሀዋሳ ከተማ ያመራል ተብሎ ቢጠበቅም አዲሱ የወልቂጤ ከተማ ፈራሚ ሆኗል፡፡

ውሉን ለማደስ የተስማማው አሳሪ አልመሐዲ በተሰረዘው የውድድር ዓመት ወልቂጤን ተቀላቅሎ ጥሩ ጊዜ ያሳለፈ ሲሆን በክለቡ ለተጨማሪ ሁለት ዓመታት ለመቆየት ተስማምቷል። አሳሪ ከወልቂጤ በፊት በድሬዳዋ ከተማ፣ ወልዋሎ እና ስሑል ሽረ ተጫውቶ አሳልፏል፡፡

👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!


© ሶከር ኢትዮጵያ