መስፍን ታፈሰ ከብሔራዊ ቡድኑ ውጪ ሆኗል

አጥቂው መስፍን ታፈሰ ከዋልያዎቹ ስብስብ ውጪ ሆኗል፡፡

በአሰልጣኝ ውበቱ አባተ አማካኝነት ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የኒጀሩ የደርሶ መልስ ጨዋታ ለአርባ አንድ ተጫዋቾች ጥሪ ሲደረግ የሀዋሳ ከተማው አጥቂ መስፍን ታፈሰ ከተጠሩት መካከል አንዱ ነበር፡፡ ሆኖም ተጫዋቹ ለሙከራ ወደ ኢኳቶሪያል ጊኒ ጳጉሜ 4-2012 አምርቶ ፉትሮ ኪንግስ ለተባለ ክለብ ለአምስት ቀናት የሙከራ ጊዜ እንደሚያሳልፍ ተገልጾ የነበረ ቢሆንም ተጫዋቹ በጊኒው ፉትሮስ ኪንግ የሙከራን ጊዜን ለማሳለፍ የተገደደው ግን አርባ ስድስት ቀናት መሆኑን ለሶከር ኢትዮጵያ ገልጿል፡፡ ክለቡ ወደ ካሜሩን ለዝግጅት ሲያመራ እሱ ግን በዛው ቀናቶችን አሳልፎ እንደመጣም ጠቁሞ ከትናንት በስቲያ ወደ ኢትዮጵያ ከመጣ በኃላ ወደ ብሔራዊ ቡድን ስብስብ ለመቀላቀል ቢሄድም የመጣበት ቀን ስላለፈ በሚል ከስብስቡ ውጪ እንደተደረገ እና ይህንንም ተከትሎ ወደ ሀዋሳ እንዳመራ ገልጿል፡፡ በዚህም ከዳዊት እስጢፋኖስ፣ አህመድ ረሺድ እና ባዬ ገዛኸኝ ቀጥሎ አራተኛው ከዋልያዎቹ ውጪ የሆነ ተጫዋችም ሆኗል፡፡

ተጫዋቹ በሀዋሳ ሁለት ዓመት ቀሪ የውል ኮንትራት ያለው ሲሆን በቀጣዮቹ ቀናት የቡድኑን ስብስብ ተቀላቅሎ ልምምድ እንደሚጀምርም ጨምሮ ነግሮናል፡፡

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉ሳንዘናጋ አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!