አትዮጵያዊያን ዳኞች የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያን ይመራሉ

ሞሮኒ ላይ ኮሞሮስ ኬንያን የምታስተናግድበት የአፍሪካ ዋንጫ አራተኛ የምድብ ማጣሪያ ጨዋታን ኢትዮጵያዊያን ዳኞች እንዲመሩ በካፍ ተመድበዋል፡፡

በምድብ ሰባት ኮሞሮስ ኅዳር 6 ኬንያን በሞሮኒ በሚገኘው ስታድ ሞሮኒ ማሎዚኒ ስታዲየም ላይ ስታስተናግድ በዓምላክ ተሰማ በመሐል ዳኝነት ይመራዋል፡፡ ለረጅም ዓመታት በወጥነት በርካታ ጨዋታዎችን የመራው በዓምላክ ባለፈው ሳምንት በኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ግማሽ ፍፃሜ የግብፁ ፒራሚድ እና ሆሮያን ጨዋታ እንደመራ ይታወሳል፡፡

በረዳት ዳኝነት ከበዓምላክ ጋር የተመደቡት ክንዴ ሙሴ እና ተመስገን ሳሙኤል ሲሆኑ አራተኛ ዳኛ በመሆን የሚያገለግለው ደግሞ ለሚ ንጉሴ መሆኑ ታውቋል፡፡ ይህን ጨዋታ የሲሼልስ ዜግነት ያላቸው ሲሞን ፊልፕ በኮሚሽነርነት ይመሩታል፡፡

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉ሳንዘናጋ አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!