ሱራፌል ዳኛቸው ለነገው ጨዋታ ይደርስ ይሆን ?

ነገ ምሽት የግብፅ ብሔራዊ ቡድንን የሚገጥመው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አማካዩን ሊያጣ ይችላል።

የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣሪያ ሁለተኛ ጨዋታዎች በአህጉራችን የተለያዩ ሀገራት እየተከናወኑ የሚገኝ ሲሆን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንም በነገው ዕለት በቢንጉ ስታዲየም የግብፅ አቻውን ይፋለማል። ለጨዋታው በጥሩ ሞራል እየተዘጋጀ የሚገኘው ብሔራዊ ቡድኑ አማካዩ ሱራፌል ዳኛቸው ከጨዋታው ውጪ እንደሆነ ተመላክቷል።

ገና የብሔራዊ ቡድን ጥሪው ሲደርሰው መጠነኛ ጉዳት የነበረበት ሱራፌል ራሱን እየጠበቀ ልምምድ እየሰራ ቆይቶ እሁድ በተደረገው የማላዊ ጨዋታ ላይ ቢሳተፍም ጉዳቱ አገርሽቶበት ዕረፍት ሰዓት ላይ ተቀይሮ እንደወጣ ይታወቃል። ጭኑ ላይ የመቀጥቀጥ ጉዳት ያስተናገደው ተጫዋቹ ከጨዋታው ማግስት በነበሩት ሁለት የልምምድ መርሐ-ግብሮች ላይም መሳተፍ ሳይችል ቀርቷል። ቡድኑ ዛሬ አመሻሽ ከጨዋታው በፊት በሚሰራው የመጨረሻ ልምምድ የሚቀየሩ ነገሮች ከሌሉ በስተቀር ተጫዋቹ አሁን ባለበት ሁኔታ ለጨዋታው ብቁ ስለማያደርገው እንደማይጫወት ተጠቁሟል።