ወልዋሎ ዓ.ዩ ቅሬታውን አሰምቷል

ወልዋሎ ዓ.ዩ ዛሬ ለፌዴሬሽኑ በላከው ደብዳቤ በዚህ ሳምንት መጨረሻ እንዲካሄድ በተወሰነው ተስተካካይ ጨዋታ እና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ያሉትን ቅሬታዎች አቅርቧል።

ክለቡ ሰፋ ያሉ ቅሬታዎቹን ለፌዴሬሽኑ ባሳወቀበት የዛሬ ደብዳቤው ለ27ኛው ሳምንት ጨዋታ ሶዶ ከደረሰ በኋላ በከተማው በነበረው አለመረጋጋት የደረሰበትን እንግልት የገለፀ ሲሆን ጨዋታው ከተሰረዘ በኃላ መቼ እንደሚደረግ ለማወቅ ያደረገው ጥረት ጉዳዩ የሚመለከታቸው የፌዴሬሽኑን አመራሮች ለማግኘት ባለመቻሉ እንዳልተሳካ አስረድቷል። ተስተካካይ ጨዋታዎቹ በሳምንቱ መጨረሻ እንዲደረጉ መወስኑን የሰሙትም ከአዳማ ጋር ለሚኖረው ጨዋታ ዝግጅት ጉዟቸውን ወደ መቐለ ካደረጉ በኋላ መሆኑን ጨምረው አስረድተዋል። በዚህ መሰረት ክለቡ ካለው የፀጥታ ችግር አንፃር ዳግም ወደ ሶዶ ሄዶ ጨዋታውን ለማድረግ እንደሚቸገር እና የተስተካካይ ጨዋታዎቹ መርሀ ግብር በጊዜ ባለመውጣቱ ለተጨማሪ እንግልት መዳረጉን ተናግሯል።

ከዚህ ውጪ ክለቡ ፌዴሬሽኑ ሊያይልኝ ይገባል ባላቸው ጉዳዮች ላይ ከመከላከያ በነበረው ጨዋታ ክስ የመሰረተባቸው ኮምሽነር ይድነቃቸው ዘውገ እና ዋና ዳኛ እያሱ ፈንቴ ጉዳይ አለመታየቱ ፣ በተጨዋች በረከት አማረ እና አሳሪ አልመሀዲ ላይ የተጣሉት ቅጣቶችን እንዲሁም በክለቡ ላይ የተላለፈው የገንዘብ ቅጣትን ጉዳይ በስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ እንዲታይ ቢጠይቅም ውሳኔው መጓተቱን እና በ12ኛው ሳምንት ከወላይታ ድቻ ጋር በነበረው ጨዋታ ያቀረበው የተጨዋች ተገቢነት ክስ አለመታየቱን አንስቷል።

የደብዳቤውን ሙሉ ሀሳብ ከዚህ በታች ማግኘት ይችላሉ።