ዛምቢያ ለምታሰናዳው የአፍሪካ ከ20 ዓመት ዋንጫ ለማለፍ በሚደረገው ማጣርያ የመልስ ጨዋታ የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን የጋና አቻውን አዲስ በተገነባው የኬፕ ኮስት ስታዲየም ነገ ይገጥማል፡፡
ብሄራዊ ቡድኑ ከማክሰኞ ጀምሮ በጋና የሚገኝ ሲሆን ወደ ጋና ከማቅናቱ በፊት ከማሊ ጋር ባደረገው የወዳጅነት ጨዋታ 5-0 ተረትቷል፡፡
ብላክ ሳተላይትስ በሚል ቅፅል ስም የሚታወቁት የጋና ከ20 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን በመጀመሪያው ዙር ያጋጠማቸውን ሽንፈት ለመቀልበስ ወደ ሜዳ እንደሚቡ ተነግሯል፡፡
በጋና ፕሪምየር ሊግ ለኩማሲው ክለብ አሻንቴ ኮቶኮ በውድድር ዓመቱ ድንቅ ብቃቱን እያሳየ የሚገኘው አጥቂው ዳዉዳ መሃመድ ጨዋታውን አሸንፈው ወደ ቀጣይ ዙር ማለፍ አላመማቸውን እንደሆነ ተናግሯል፡፡ “በመጀመሪያው ዙር ስለተጋጣሚያችን የነበረን መረጃ እምብዛም ነበር፡፡ ከጨዋታው በኃላ የኢትዮጵያን ጠንካራ እና ደካማ ጎን ለማወቅ ችለናል፡፡ ስንዘጋጅ የነበረው የኢትዮጵያ ድክመትን እንዴት መጠቀም እንችላለን የሚለው ላይ ነበር፡፡
“እግርኳስ ስለሆነ ማንኛውም ነገር ሊያጋጥም ይችላል፡፡ እኔ ላለገባ እችላለው ኳስ አመቻችቼ ላቀብል እችላለው ዋናው ቁም ነገር ጋናን ወደ ቀጣዩ ዙር ማሳለፍ ነው፡፡”
ዳዉዳ በክለብ ጨዋታ ያሳየው ብቃት በብሄራዊ ቡድኑ መድገም እንደሚፈልግም ጨምሮ ገልጿል፡፡ “ጠንክሬ ልምምዶችን እየሰራው ነው፡፡ በክለብ የነበረኝን ብቃት ወደ ብሄራዊ ቡድን ማምጣት እፈልጋለው” ብሏል፡፡
የብላክ ሳተላይትስ አሰልጣኝ መስኡድ ዲዲ ድራማኒ ዳዉዳን ለአዲስ አበባው ጨዋታ ማካተታቸውን ተከትሎ ከኮቶኮ ክለብ ሃላፊዎች ከፍተኛ ትችት ሲደርስባቸው ነበር፡፡ ዲዲ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ከመምጣታቸው በፊት ኮቶኮን ለሁለት የጋና ፕሪምየር ሊግ አሸናፊነት አብቅተዋል፡፡
ረዳት አሰልጣኙ ያው ፕሪኮ በበኩሉ ቡድኑ አዲስ አበባ ላይ የሰራቸውን ስህተቶች ላለመድገም ወደ ሜዳ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ከ20 አመት በታች ብሄራዊ ቡድን በመጀመሪያው ጨዋታ አዲስ አበባ ላይ በአሜ መሃመድ ሁለት ግቦች 2-1 ማሸነፉ ይታወሳል፡፡
(መረጃውን ለሶከር ኢትዮጵያ ያደረሰው የጋና ከ20 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን የሚዲያ ሃላፊ ፍሬድሪክ አቼምፖንግ ነው)