የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መካከለኛ – ሰሜን ዞን ዛሬ ተጠናቋል፡፡ ሎዛ አበራም አስደናቂ የግብ ማስቆጠር ሪከርድ ይዛ አጠናቃለች፡፡
የዞኑ የመጨረሻ ሳምንት ጨዋታዎች ባለፈው ሳምንት የተጠናቀቁ ቢሆንም ሳይካሄድ ተዘሎ የነበረው የ18ኛ ሳምንት ዛሬ ተካሂዷል፡፡
2 ጨዋታ እየቀረው የዞኑ ቻምፒዮን መሆኑን ያረጋገጠው ደደቢት ዛሬ ከሙገር ሲሚንቶ ባደረገው ጨዋታ 6-0 አሸንፏል፡፡ ከደደቢት የድል ግቦች አምስቱን ከመረብ ያሳረፈችው ሎዛ አበራ ናት፡፡
በ20 ጨዋታዎች 47 ግቦችን ከመረብ ያሳረፈችው ሎዛ ከዚህ ቀደም በሽታዬ ሲሳይ ተይዞ የነበረውን የከፍተኛ ግብ አግቢነት ሪከርድ መስበር ችላለች፡፡
ደደቢት 79 የግብ ልዩነቶች በመያዝ በስኬት እንዳጠናቀቀው ሁሉ እቴጌ ዘንድሮም 87 የግብ እዳ በመሰብሰብ የመጨረሻ ደረጃን ይዞ አጠናቋል፡፡ እቴጌ ባለፈው የውድድር ዘመን 99 የግብ እዳ ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው፡፡
የአምናው ቻምፒዮን ንግድ ባንክ ካለፉት አመታት የወረደ ውጤት ሲያስመዘግብ መከላከያ ደግሞ እጅግ ከፍተኛ መሻሻል ያሳየ ክለብ ሆኗል፡፡
የሳምንቱ ውጤቶች
ቅዳሜ ሰኔ 4 ቀን 2008
እቴጌ 0-1 ኢትዮ ኤሌክትሪክ
እሁድ ሰኔ 5 ቀን 2008
ልደታ ክ/ከተማ 1-3 ዳሽን ቢራ
ኢትዮጵያ ቡና 1-3 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
ሰኞ ሰኔ 6 ቀን 2008
ቅዱስ ጊዮርጊስ 2-1 ቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ
ሙገር ሲሚንቶ 0-6 ደደቢት
ከሁለት ዞኖች የተውጣጡ 10 ክለቦች የሚሳተፉበት የማጠቃለያ ውድድርም በቀጣይ ሳምንት በሀዋሳ አስተናጋጅነት ይጀመራል፡፡
ተሳታፊ ክለቦች
ከመካከለኛ – ሰሜን ዞን
ደደቢት ፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፣ መከላከያ ፣ ዳሽን ቢራ ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ
ደቡብ – ምስራቅ ዞን
ሀዋሳ ከተማ ፣ ሲዳማ ቡና ፣ ድሬዳዋ ከተማ ፣ አርባምንጭ ከተማ