የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን ዛምቢያ ለምታስተናግደው የአፍሪካ ከ20 ዓመት በታች ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ የመልስ ጨዋታውን ከጋና አቻው ጋር በኬፕ ኮስት ከተማ በሚቀጥለው ሳምንት ያደርጋል፡፡
ለመልሱ ጨዋታ ይረዳቸው ዘንድም ከማሊ ከ20 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድንን በአቋም መለኪያ ጨዋታ ለመግጠም ወደ ባማኮ አምርቷል፡፡
የቡድን መሪው ቾል ቤል (ኢ/ር) ወደ ማሊ ከማቅናታቸው በፊት በተዘጋጀ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ማሊ በቅርቡ ከጋና ጋር በመጫወቷ ለወዳጅነት ጨዋታ እንደመረጧት ተናግረዋል፡፡
“እንደስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ዕቅድ አቅርበን ይህ ቡድን ከጋናው ጨዋታ በፊት የአቋም መለኪያ ጨዋታ ያፈስፈልገዋል ብለን ወስነን ጨዋታዎችን ስንፈልግ ነበር፡፡ ሁለት ሃገራትንን አግኝተን ነበር ፤ ማሊ እና ናይጄሪያን፡፡ ናይጄሪያ ካላባር ላይ ከቡሩንዲ ስለሚጫወቱ ከእኛ ጋር መጫወት እንደማይችሉ ነግረውናል፡፡ ማሊ የእኛን ጥያቄ ተቀብሎ ከእኛ ጋር ለመጫወት ፍቃደኛ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ማሊን የመረጥንበት ምክንየት ከጋና ጋር በቅርቡ ተጫውቶ ነበር፡፡ ስለዚህም አቋማችንን ለመለካት ለእኛ ጥሩ ይሆናል ብለን መርጠናል፡፡ ” ብለዋል፡፡
ቡድኑ 23 ተጫዋቾችን በመያዝ ትላንት ረፋድ ወደ ማሊ የተጓዘ ሲሆን ከ6:30 በረራ በኋላ ባማኮ ደርሶ በኮሎምበስ ሆቴል አርፏል፡፡
ትላንት የ40 ደቂቃ ልምምድ ሲያደርግ ዛሬ ደግሞ ቀለል ያለ ልምምድ ሰርተዋል፡፡
የወዳጅነት ጨዋታው ዛሬ ምሽት 02:00 ባማኮ ስታድየም ላይ ይደረጋል፡፡ በማግስቱ ረቡዕም ወደ ጋና የሚያቀኑ ይሆናል፡፡
ብሄራዊ ቡድኑ ወደማሊ ከማቅናቱ በፊት ስለዝግጅት እና ተያያዥ ጉዳዮች የብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ ግርማ ሃብተዮሃንስ፣ አምበሉ ዘሪሁን ብርሃኑ እና የቡድን መሪው ኢንጂነር ቾል ቤል በኢትዮጵያ ሆቴል ከሰጡት መግለጫ ዋና ዋናዎቹን እንደሚከተለው አቅርበንላችኋል፡፡
ግርማ ሃብተዮሃንስ
” እንደሚታወቀው ባለፈው ጊዜ ከጋና ጋር አዲስ አበባ ላይ ጨዋታችንን ካደረግን በኃላ ተጫዋቾቻችን በሃገር ውስጥ ውድድር ላይ ተሳትፎ ማድረግ ስለነበረባቸው እንደገና ወደ ክለባቸው እንዲመለሱ ተደርጎ ተጫውተዋል፡፡ እኛም ከፍተኛ ፉክክር የነበረበትን ጨዋታ ጅማ ጨዋታዎች ተመልከተናል በጎደሉን ተጫዋቾች ላይም ለመምረጥ ዕድል ተፈጥሮልናል፡፡ ተጨማሪ ተጫዋቾችን በማምጣጥ ያሉትን ነባር ተጫዋቾች በመያዝ ዝግጅታችን በአዳማ ተሰባስበን አድርገናል፡፡ በአሁኑ ሰዓት 23 ተጫዋቾች አሉን፡፡ ከባለፈው ስብስብ ሶስት ተጨማሪ ተጫዋቾች ጨምረን ቡድናችንን ለጋና ግጥሚያ አዘጋጅተናል፡፡ ”
ኢንጂነር ቾል ቤል
” ከጋናው ጨዋታ መልስ ዝግጅት ለመቀጠል ነበር የታሰበው፡፡ ነገር ግን የሃገር ውስጥ ውድድሮች አስገድዶን ተጫዋቾች ለአንድ ሳምንት ወደ ክለቦቻቸው ሄደዋል፡፡ ቡድኑ የተሟላ እንዲሆን እኛ ከአሰልጣኙ ጋር በመነጋገር ከጋና አየር ተነስተን አዳማ በማቅናት ተዘጋጅቷል፡፡
ዘሪሁን ብርሃኑ
” ከጋና ጋር ያደረግነውን ጨዋታ 2-1 ካሸነፍን በኃላ በዝግጅት ለመቆየት አስበን ነበር፡፡ ነገር ግን ከክለቦቻችን በተደረገልን ጥሪ ምክንያት ወደየክለቦቻችን ተመልሰን ጨዋታዎችን አድርገን ነበር የመጣነው፡፡ በክለቦቻችን በነበረን ቆይታ ሰፊ የሆነ የልምምድ ግዜ አልነበረንም፡፡ የነበረን አናሳ ግዜ ነበር፡፡ ጥቂት የኮርዲናሽን ልምምዶችን በቂ ነው ባይባልም አድርገናል፡፡ የጋና ዓየርንም እንድንላመድ ወደ አዳማ አቅንተን ልምምዶችን ሰርተናል፡፡ በአዳማ በነበረን ቆይታ አዳዲስ ከተመረጡት ጋር የምንግባባበትን መንገድ ተፈጥሮ የተለያዩ የኮርዲኔሽን ልምምዶችን አድርገናል፡፡ ከማሊ ጋር የምናደርገው ጨዋታ ለቀጣይ የጋና ግጥሚያ ጥሩ ልምድ ይሆነናል፡፡ “