ባልታወቀ ምክንያት ጠፍቶ የነበረው ተጫዋች ወደ ክለቡ ተመልሷል

ባልታወቀ ምክንያት ከቡድኑ ተለይቶ የሰነበተው ናሚቢያዊው የወልዋሎ ተጫዋች በድጋሚ ቡድኑን ተቀላቅሏል።

በውድድር ዓመቱ መጀመርያ የናሚብያው ቱራ ማጂክ ለቆ ወልዋሎን በመቀላቀል በአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ ያሳየው ናሚብያዊ ጁንያስ ናንጋጂቦ ቡድኑ ሰበታ ከተማን ካሸነፈ በኃላ ባልታወቀ ምክንያት ከቡድኑ ተለይቶ ወደ ያልታወቀ ቦታ ቢጠፋም ከቀናት በኋላ ወደ ቡድኑ ተመልሷል። ወልዋሎዎች ወላይታ ድቻን ሲያሸንፉ ከቡድኑ ጋር ያልነበረው ይህ አጥቂ በትናንትናው ዕለት ወደ መቐለ አምርቶ ዛሬ አመሻሽ ከቡድኑ ጋር ልምምድ ጀምሯል።

ከዚ በፊትም በ2009 የውድድር ዓመት ሁለተኛ ዙር ሙሉዓለም ጥላሁን ወልዋሎዎች ከኢትዮጵያ ቡና ከተጫወቱ በኃላ ከቡድኑ ጠፍቶ በክለቡ እስከ መከሰስ ደርሶ እንደነበር ይታወሳል። ከዚ ቀደም በኢትዮ-ኤሌክትሪክ በአማካይ ስፍራ ሲጫወት የነበረው ታሚ ኩፔም በተመሳሳይ ከክለቡ ጋር ውል እያለበት ስድስት መቶ ሺህ ብር ይዞ መጥፋቱም ይታወሳል፡፡


© ሶከር ኢትዮጵያ