ናይጄርያዊው የቅዱስ ጊዮርጊስ የመስመር አማካይ ሳሚ ሳኑሚ ለደደቢት መፈረሙን ፕላኔት ስፖርት ዘግቧል፡፡
በተጠናቀቀው የውድድር ዘመን ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ቻምፒዮን የሆነው ሳሙኤል ሳኑሚ ከደደቢት ጋር በዝውውር ጉዳዮች ላይ መነጋገር ከጀመረ ቆየት ማለቱና ሁለቱ ቡድኖች በኢትዮጵያ ዋንጫ ፍፃሜ ከመጫወታቸው ቀደም ብሎ ከስምምነት ላይ መድረሳቸው ተነግሯል፡፡ ሳኑሚ በጨዋታው ላይ ግብ አስቆጥሮ ደስታውን አለመግለፁም በዚህ ምክንያት ነው ተብሏል፡፡
ናይጄርያዊው ባለፈው ክረምት ከመብራት ኃይል ወደ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ15 ሺህ ዶላር የፊርማ ክፍያ የፈረመ ሲሆን በአጥቂ እና በመስመር አማካይነት በርካታ ጨዋታዎች ላይ ተሰልፏል፡፡
ሳሙኤል አቤይ ‹‹ ሳኑሚ ›› የዝውውር ሂሳቡ ባይጠቀስም እስከ 850 ሺህ የኢትዮጵያ ብር የሚገመት የፊርማ ክፍያ እንደተቀበለ ተነግሯል፡፡ ሳሚ ለደደቢት ዛሬ እንደሚፈርም ቢጠበቅም ነገ በፌዴሬሽኑ ፅህፈት ቤት በመገኘት ለሰማያዊው ጦር በመፈረም ለእረፍት ወደ ሃገሩ ናይጄርያ ያቀናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ሳሚ ያለፉትን 3 የውድድር ዘመናት በመብራት ኃይል እና በቅዱስ ጊዮርጊስ መለያ በፕሪሚየር ሊጉ ተጫውቷል፡፡