ሀዋሳ ከተማ ቶጓዊ አጥቂ አስፈርሟል

ሀዋሳ ከተማ ቶጓዊው አጥቂ ክዎሚ ፎቪ አጉዊዲን ማስፈረሙ ታውቋል።

ሀዋሳ ከተማ በዝውውር መስኮቱ የተቀዛቀዘ ጊዜን በማሳለፍ እስካሁን አንድ ተጫዋች ብቻ አስፈርሞ የቆየ ሲሆን የአጥቂ መስመሩን ለማጠናከር ፎቪ አጉዊዲን የተባለ ተጫዋች በአንድ ዓመት ውል አስፈርሟል። ከአጥቂ በተጨማሪ በመስመር ተጫዋችነት መሰለፍ የሚችለው ተጫዋቹ ከዚህ ቀደም ወደ ሀዋሳ በመምጣት ለመፈረም ተስማምቶ የነበረ ቢሆንም የተሻለ ክፍያ በማግኘቱ ወደ ባህሬን ሊግ አምርቶ እንደነበር ይታወሳል።

የ26 ዓመቱ አጥቂ የጋናው ኸርትስ ኦፍ ኦክ፣ የቡርኪና ፋሶው ሳንቶስ፣ የባህሬኑ አል አህሊ እና የሀገሩ ክለብ ዳይናሚክ ቶጎሊስ ሎሜ የተጫወተባቸው ክለቦች ናቸው።

ፉቪ አጉዊዲ ከሀገሩ ዜጋ ሶሆሆ ሜንሳህ ጋር በሀዋሳ ሲገናኝ በቡድኑ ውስጥ የሚገኝ ሶስተኛ የውጪ ዜጋ ሆኗል።