ዝውውር | አህመድ ረሺድ ወደ ድሬዳዋ ከተማ አምርቷል

የኢትዮጵያ ቡናው የመስመር ተከላካይ አህመድ ረሺድ ከክለቡ ጋር ያለው ውል መጠናቀቅን ተከትሎ ማረፊያው ድሬዳዋ ከተማ ሆኗል፡፡

በ2006 ደደቢትን ለቆ ኢትዮጵያ ቡናን የተቀላቀለው አህመድ ረሺድ በፍጥነት በእለቡ የቋሚ ተሰላፊነት እድልን ያገኘ ሲሆን በግራ እና በቀኝ እንዲሁም በመል ተከላካይ ስፍራ ላይ ክለቡን አገልግሏል፡፡ ሆኖም በተጠናቀቀው የውድድር ዘመን የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ላይ ከክለቡ ደጋፊዎች ጋር በፈጠረው ውዝግብ በቡና ቤት የመቆየት እድሉ አጠራጣሪ ሀኖ የቆየ ሲሆን ክለቡ በይፋዊ የፌስቡክ ገጹ ተጫዋቹ በቡና ለመቆየት በቃል ደረጃ መስማማቱን ቢገልፅም የቀድሞ ክለቡ ደደቢትን ጨምሮ ከተለያዩ ክለቦች ዝውውር ጋር ስሙ ሲያያዝ ቆይቶ በመጨረሻም ወደ ድሬዳዋ ከተማ ማምራቱን ሶከር ኢትዮጵያ ከተጫዋቹ አረጋግጣለች፡፡

አህመድ ረሺድ በድሬዳዋ ለአንድ የውድድር ዘመን ለመቆየት የተስማማ ሲሆን በ1.2 ሚልዮን ብር የክለቡ ከፍተኛው ተከፋይ ተጫዋች መሆኑም ተነግሯል፡፡

ድሬዳዋ ከተማ ከአስከፊ የውድድር ዘመን በኋላ በመጨረሻ ጨዋታ መትረፉን ተከትሎ በቀጣዩ የውድድር ዘመን ጠንካራ ቡድን ለመመስረት ከሌሎቹ ክለቦች ቀድሞ በርካታ ተጫዋቾችን እያዘዋወረ ይገኛል፡፡ ከወዲሁም አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ከግማሽ ደርዘን በላይ ተጫዋቾችን ለማስፈረም መስማማታቸው ታውቋል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *