አሰልጣኝ ገብረ መድህን ረዳት አሰልጣኛቸውንና የግብ ጠባቂ አሰልጣኙን ዛሬ ለፌዴሬሽኑ ይፋ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ሶከር ለጉዳዮ ቅርበት ካላቸው አካላት እንዳረጋገጠችው የሲዳማ ቡናው አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራውን ረዳት አሰልጣኝ ፣ የኢትዮዽያ ቡናው ውብሸትን ደሳለኝን ደግሞ የግብ ጠባቂዎች አሰልጣኝ ማድረጋቸው ታውቋል፡፡
ፌዴሬሽኑ የገብረመድህን ረዳቶችን ጉዳይ ይፋ ያላደረገ ሲሆን አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ከአሰልጣኝ ገብረመድህን ጋር በስልክ መነጋገራቸውና ጉዳዩን ከዳር ለማድረስ ከይርጋለም ወደአዲስ አበባ እየመጡ መሆኑም ታውቋል፡፡
የግብ ጠባቂዎች አሰልጣኝ ውብሸት ደሳለኝ በበኩላቸው ጉዳዩን ከሰዎች እንደሰሙና አሁን ባለው ሁኔታ ምንም ማለት እንደማይችሉ ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጊዜያዊ የፅህፈት ቤት ሃላፊና የሕዝብ ግኑኝነት ሀላፊ አቶ ወድምኩን አላዩ ከፊፋ ጠቅላላ ጉባኤ መልስ ቢሮ የገቡት ዛሬ በመሆኑ ስለጉዳዩ የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ገልፀዋል፡፡
በጉዳዩ ዙርያ የአሰልጣኝ ገብረመህድንን አስተያየት ለማካተት ያደረግነው ጥረት ያልተሳካ ሲሆን ስለ ብሄራዊ ቡድን ሹመታቸው ፣ የመረጧቸው የአሰልጣኝ ቡድን አባላት እና ስለቀጣይ የኢትዮዽያ ብሔራዊ ቡድን እጣፈንታ በቅርቡ ጠቅለል ያለ ጋዜጣዊ መግለጫ ይሰጣሉ ተብሏል፡፡
በተያየዘ ዜና ለብሄራዊ ቡድኑ የተሾሙት አሰልጣኞች የክለብ ስራቸውንም ደርበው እንደሚሰሩ ቢጠበቅም ከውስጥ አዋቂ ምንጮቻችን እንደሰማነው አሰልጣኝ ገብረመድን እና አሰልጣኝ ዘላለም ከሁለት የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ በኋላ ሙሉ ለሙሉ የክለብ አሰልጣኝነታቸውን በመተው ሙሉ ትኩረታቸውን በብሄራዊ ቡድኑ ላይ ያደርጋሉ፡፡