የ2007 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ግማሽ የውድድር ዘመን እሁድ ከሚደረጉት ሶስት ተስተካካይ ጨዋታዎች በኋላ ይጠናቀቃል፡፡ በ3ኛው ሳምንት መደረግ የነበረባቸው ጨዋታዎች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ በነበረው ዝግጅት ምክንያት ለእሁድ ጥር 24 ቀን 2007 ዓ.ም መተላለፋቸው ይታወቃል፡፡
ቦዲቲ ላይ በ9፡00 ወላይታ ድቻ ቅዱስ ጊዮርጊስን ያስተናግዳል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ይህንን ጨዋታ በድል ከተወጣ ሲዳማ ቡናን በግብ ልዩነት በልጦ የመጀመርያውን ዙር የሊጉ አናት ላይ ሆኖ ያጠናቅቃል፡፡ 21 ነጥቦችን ይዞ 4ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው ወላይታ ድቻ ካሸነፈ ከመሪው ሲዳማ ቡና የሚኖረውን የነጥብ ልዩነት ወደ 3 ዝቅ የማድረግ እድል ይኖረዋል፡፡
ሀዋሳ ላይ ወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኘው ሀዋሳ ከነማ ደደቢትን 9፡00 ላይ ያስተናግዳል፡፡ ሁለቱም ቡድኖች አንደኛው ዙር ሳይጠናቀቅ አሰልጣኞቻቸውን ያሰናበቱ ሲሆን ጨዋታውን አሽንፈው የአንደኛውን ዙር ማጠርንደኛውንውንናቀቅ ለሁለቱም ወሳኝ ነው፡፡ ሁለቱ ቡድኖች ከ4 ቀናት በኋላ በኢትዮጵያ ዋንጫ አበበ ቢቂላ ስታድየም ላይ በድጋሚ ይፋለማሉ፡፡
በ10 ሰአት የአዲስ አበባዎቹ ኢትዮጵያ ቡና እና መብራት ኃይል በአበበ ቢቀላ ስታድየም ይፋለማሉ፡፡ ቡና በ21 ነጥብ 3ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ይህን ጨዋታ በድል ከተወጣ ከመሪው ያለውን ርቀት በ3 ነጥቦች ያጠባል፡፡ ካለፉት 5 ጨዋታዎች ድል የራቀው መብራት ኃይል ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይህንን ጨዋታ ማሸነፍ ይጠበቅበታል፡፡
ፌዴሬሽኑ የሁለተኛውን ዙር የጨዋታ ቀናት ያላሳወቀ ሲሆን በአዲስ አበባ ስታድየም ከሚደረገው የአፍሪካ ወጣቶች አትሌቲክስ ቻምፒዮና መጠናቀቅ በኋላ በመጋቢት ወር ሊጀመር እንደሚችል ይገመታል፡፡