ኮንጎ ሪፐብሊኩ ኤሲ ሊዮፓርድስ ባለፈው ሳምንት በሜዳው የደረሰበትን የ 1-0 ሽንፈት ቀልብሶ ወደ ካፍ ቻምፒየንስ ሊግ ምድብ ድልድል ለመግባት ነገ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከባድ ፈተና ይገጥመዋል፡፡
ኤሲ ሊዮፓርድስ 23 ተጫዋቾችን ጨምሮ በአጠቃላይ 42 የልዑካን ቡድን በመያዝ ትላንት ማምሻውን አዲስ አበባ በመግባት ማረፊያውን ጁፒተር ሆቴል ያደረገ ሲሆን አዲስ አበባ ከገባ በኋላ የመጀመርያውና የመጨረሻ የሆነውን ልምምድ ዛሬ 10:00 ላይ በአዲስ አበባ ስታድዮም አከናውኗል ።
ለ1:30 በቆየው ልምምድ በፈጣን እንቅስቃሴ የተጋጣሚ ቡድንን አጨዋወት የመቋጣጠር እና ኳስ የመጠንቅ ፣ በመስመር የማጥቃት አጨዋወትን ሲለማመዱ ተስተውሏል፡፡
ከጉዳት ጋር በተያያዘ በመጀመርያው ጨዋታ ላይ በአጥቂ መስመር ላይ ጫና በመፍጠር የፈረሰኞቹን የተከላካይ መስመር ሲረብሽ የነበረው የዛምቢያዊ አጥቂ ዊንሰን ካሉንጎ ቁርጭምጭሚቱ ላይ ባጋጠመው ጉዳት በነገው ጨዋታ የመሰለፉ ጉዳይ አጠራጣሪ ነው፡፡ ዊንስተን ከቡድኑ አባላት ጋር አዲስ አበባ ቢገኝም በዛሬው ልምምድ ላይ ቁጭ ብሎ ከማየት በዘለለ በልምምዱ ላይ መሳተፍ አልቻለም። የተቀሩት የቡድኑ ተጨዋቾች ግን ለነገው ጨዋታ ዝግጁ መሆናቸውን ለማወቅ ችለናል።
የኤሲ ሊዮፓርድስ አሰልጣኝ ሮዥር ኤሊ ኑሲዬቴ አስተያየት
ስለ መጀመርያው ጨዋታ
እጅግ በጣም ጥሩ ጨዋታ ነበር። ቅዱስ ጊዮርጊስ በቴክኒክም ፣ በታክቲክም ፣ በአካል ብቃትም እጅግ በጣም የተደራጀ ቡድን ነው። እኛ ቅዱስ ጊዮርጊስን በዚህ ሁኔታ አልጠበቅነውም ፣ አሁን ግን የመልስ ጨዋታው እንደመሆኑ መጠን በሚገባ ተዘጋጅተናል፡፡ ስለዚህ የመልሱ ጨዋታ ለሁለታችንም ቀላል አይሆንም።
ከነገ ጨዋታ ምን እንጠብቅ?
ለጨዋታው የሚሆን የተለየ ስትራቴጂ በመንደፍ ሜዳ ላይ ለመተግበር እንገባለን፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ጥንካሬ ፈታኝ ቢያደርግብንም ሁሉን ነገር ተቋቁመን እንወጣለን። በነገው ጨዋታ ከሁለት ወዳጅ ሀገር ክለቦች ግጥሚያ ሰላማዊ እግር ኳስ እንጠብቃለን፡፡ የተሻለው ቡድንም አሸንፎ ወደ ምድብ ይገባል፡፡