ወልዲያ | አዳሙ መሐመድ ልምምድ ሲጀምር ምክትል አሰልጣኙ ወደ ስራቸው ሊመለሱ ይችላሉ

በጉዳት ምክንያት በዘንድሮ አመት ፈታኝ ግዜ ያሳለፈው የወልዲያው ጋናዊ ተከላካይ አዳሙ መሐመድ ለህክምና ወደ ሀገሩ ጋና ካቀና በኋላ በፍጥነት በማገገሙ ዳግም ወደ ወልድያ ተመልሶ ልምምድ መስራት መጀመሩ ታውቋል። አሁን የጤንነቱ ሁኔታ የተሻለ መሆኑን የሚናገረው አዳሙ መሐመድ በቅርቡ ሙሉ ለሙሉ ወደ ጨዋታ እንደሚመለስ ተናግሯል። የአዳሙ በጉዳት መራቅን ተከትሎ የተከላካይ መስመሩ ለሳሳው ክለቡም መልካም ዜና ሆኗል።

በሌላ ዜና ስራቸውን በራሳቸው ፍቃድ የለቀቁት ምክትል አሰልጣኙ ኃይማኖት ግርማ ዳግም ወደ ቡድኑ በሚመለሱበት ጉዳይ ላይ ከቡድኑ አመራሮች ጋር በቅርቡ እንደሚመክሩ የታወቀ ሲሆን ምክከሩ መልካም ነገር ይዞ እንደሚመጣ እና ቡድኑን በቀጣይ በዋና በአሰልጣኝነት ሊመሩ እንደሚችሉ ተገምቷል።

ወልዲያ ማክሰኞ ከመቐለ ከተማ ጋር በአዲስ አበባ ስታድየም ለሚያደርገው ጨዋታ ዛሬ በቅዱስ ጊዮርጊስ የልምምድ ሜዳ ማምሻውን ልምምድ በሰራበት ወቅት አሰልጣኝ ዘማርያም ወ/ ጊዮርጊስ ያልተገኙ ሲሆን የህክምና ክትትል እያደረጉ ከመሆናቸው ጋር ተያይዟል። ሆኖም አሰልጣኙ በቀጣይ ከቡድኑ ጋር አብሮ ይቀጥላሉ ተብሎ እንደማይገመት እየተገለፀ ይገኛል።

ፎቶ – Woldia SC