የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ በሳምንቱ መጀመርያ ይፋ ይሆናል

ሰሞኑን ሲያነጋግር የቆየው የዋልያዎቹ ቀጣይ አሰልጣኝ ሹመት ሰኞ በሚሰጥ ጋዜጣዊ መግለጫ እልባት እንደሚያገኝ ተገለፀ፡፡

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በሐምሌ 2012 የመጨረሻው ቀን ላይ ለሁሉም የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኞች ውድድሮች ስለሌሉ ውል አላራዝምም በማለት ውሳኔ ካስተላለፈ ከሳምንታት በኃላ ካፍ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ቀናትን ይፋ በማድረጉ እና ውድድሩም እየቀረበ የመጣ ከመሆኑ አንፃር የእግርኳሱ ቤተሰብ በአፋጣኝ የአሰልጣኝ ሹመት ይደረግ በሚል ሲነጋገርበት ቆይቷል፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽንም ለብሔራዊ ቴክኒክ ኮሚቴ የአሰልጣኝ ምርጫን እንዲሁም ቴክኒካል ጉዳዮችን ተመካክሮ ምክረ ሀሳብ ለሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ሜስተላለፉን ገልፆ እንደነበር ይታወቃል። የቴክኒክ ኮሚቴውም የደረሰበትን ውጤት ጨርሶ አሰልጣኝ አብርሀም መብራቱ ይቀጥሉ በሚል ለውሳኔ ቢያቀርብም የሥራ አስፈፃሚው በተቃራኒው የቀረበለትን ወደ ጎን በመተው አሰልጣኝ ውበቱ አባተን መርጧል የሚሉ መረጃዎች ወጥተዋል። የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን እስካሁን የዋልያዎቹ አሰልጣኝ ማን እንደሆነ ባይገልፅም የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን የፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን ሰኞ የቀጣዩን አሰልጣኝ ቅጥር ይፋ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል።

“ከአሰልጣኝ ቅጥር ጋር በተያያዘ ፌዴሬሽኑ የጀመራቸው ሥራዎች አሉ፡፡ እነኚህ እየተሰሩ ያሉ ሥራዎች ሲያልቁ ለሚዲያ እና ለህዝቡ በመግለጫ እናሳውቃለን። በርካታ ነገሮች በጭምጭምታ ደረጃ እየተሰማ ነው፤ እኛም እየተመለከትን ነው። ሲናፈሱ የነበሩ ነገሮች ምን ያህል እውነት ናቸው ፌድሬሽኑ ከውሳኔዎቹ ጋር በተያያዘ ያየቸው ጉዳዮች ምንድን ናቸው? ምን ነበር ውይይቱ ላይ የነበረው? የሚለውን ምንም ሳናስቀር በመግለጫ እንገልፃለን። ይሄ ደግሞ ከሰኞ አያልፍም። ያለቀውን የአሰልጣኝ ሹመት እኛው እንገልፃለን። አሁን የሚወሩትን ግን እንደማንኛውም እየሰማን እና እያየን ነው፡፡”

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!