ከሴፕቴምበር 30 – ኦክቶበር 21,2016 ጆርዳን ላይ ለሚስተናገደው ከ17 አመት በታች ሴቶች የአለም ዋንጫ አፍሪካን የሚወክሉ 3 ሃገራት ታውቀዋል፡፡ በሴቶች እግርኳስ የአፍሪካ የበላይነታቸውን በተደጋጋሚ ያስመሰከሩት የምዕራብ አፍሪካ ሃገራትም በማጣርያው የበላይ ሆነዋል፡፡
በመጀመርያው የማጣርያ ዙር ኢትዮጵያን በድምር ውጤት 3-3 (ካሜሩን በመለያ ምቶች አሸንፋለች) በመርታት ወደ ተከታዩ የማጣርያ ዙር ያለፈችው ካሜሩን ግብፅን በድምር ውጤት 6-1 በማሸነፍ የአለም ዋንጫ ትኬቷን ቆርጣለች፡፡ ካሜሩን በመጀመርያው ጨዋታ በሜዳዋ 2-1 ያሸነፈች ሲሆን በመልሱ ጨዋታ ከሜዳዋ ውጪ ባልተጠበቀ ሁኔታ 4-0 ማሸነፍ ችላለች፡፡
ጋና በሞሮኮ ላይ የግብ ናዳ በማውረድ ወደ አለም ዋንጫው አልፋለች፡፡ ከሜዳዋ ውጪ 4-0 በማሸነፍ ወደ አክራ የተመለሰችው ጋና በመልሱ ጨዋታ 6-0 በማሸነፍ በ10-0 ድምር ውጤት አልፋለች፡፡
ሌላዋ የምዕራብ አፍሪካ ሃገር ናይጄርያ ደቡብ አፍሪካን በመርታት በእያንዳንዱ የአለም ዋንጫዎች ላይ የመሳተፍ ሪከርዷን አስጠብቃለች፡፡ ሌጎስ ላይ 6-0 አሸንፋ ወደ ጆሃንስበርግ ያቀናችው ናይጄርያ 1-0 በማሸነፍ በ7-0 ድምር ውጤት የአለም ዋንጫውን ተቀላቅላለች፡፡

የአለም ዋንጫው ተሳታፊ ሃገራት የሚከተሉት ናቸው
ኮንካካፍ (ሰሜን እና መካከለኛው አሜሪካ ፣ 3)
ካናዳ ፣ ዩናይትድ ስቴትስ ፣ ሜክሲኮ
ኮሜቦል (ደቡብ አሜሪካ ፣ 3)
ቬኔዝዌላ ፣ ብራዚል ፣ ፓራጓይ
ካፍ (አፍሪካ ፣ 3)
ጋና ፣ ናይጄርያ ፣ ካሜሩን
ኤኤፍሲ (ኤሽያ ፣ 3)
ጆርዳን ፣ ሰሜን ኮርያ ፣ ጃፓን
ኦኤፍሲ (ኦሽንያ ፣ 1)
ኒውዝላንድ
ዩኢኤፍኤ (አውሮፓ ፣ 3)
የማጣርያ ጨዋታዎች አልተጠናቀቁም፡፡