የአሰልጣኞች አስተያየት | ደቡብ ፖሊስ 2-0 አዳማ ከተማ 

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ 23ኛ ሳምንት ጨዋታ ሀዋሳ ላይ ደቡብ ፖሊስ አዳማ ከተማን አስተናግዶ 2-0 ካሸነፈ በኋላ የደቡብ ፖሊሱ አሰልጣኝ ገብረክርስቶስ ቢራራ ከሶከር ኢትዮጵያ ጋር ቆይታ ሲያደርጉ የአዳማ ከተማው አሰልጣኝ አስቻለሁ ኃይለሚካኤል ግን አስተያየት ሳይሰጡ ቀርተዋል።

“ጨዋታውንም እና ኳሱንም ተቆጣጥረነዋል”
ገብረክርስቶስ ቢራራ (ደቡብ ፖሊስ)

ስለጨዋታው

“የዛሬው ጨዋታ በጣም ጥሩ ነበር። ምክንያቱም ሁለት ነገሮችን አሳክተናል። ጨዋታውን እና ኳሱን ተቆጣጥረናዋል። ጨዋታውን መቆጣጠር እንጂ ኳስን ብቻ መቆጣጠር ውጤታማ አያደርግም። ጨዋታውን ስለተቆጣጠርንም ነው ብዙ አጋጣሚዎችን ያልፈጠሩብን። ተጫዋቾቻችን የተሰጣቸውን ኋላፊነት በሚገባ ተወጥተዋል። ጥሩ ተጫውተናል። በጨዋታ እና ግብ በማግባት በጣም የተሻልን ስለነበርን ውጤታማ ሆነናል።

አጥቅቶ ስለመጫወት

እኛ ቀጣዮችን ጨዋታዎች በጥንቃቄ ነው መጫወት ያለብን። በዚህ ስዓት እንድ ጨዋታ ላይ ነጥብ ጣልን ማለት ከባድ ነው። ምክንያቱም ሁላችንም ተፋፍረን ነው ያለነው። ስለህ ሁልጊዜ የሚያሰፈልገን ነገር ኃላፊነቱን ወስደን አጥቅተን መጫወት ነው። ለዛም ነው በሶስት አጥቂዎች የምንጫወተው። አጥቅተን ከተጫወትን ውጤታማ እንሆናለን፤ መፍራት የለብንም። እግር ኳስ ብዙ ስለተጠነቀቅክ ብቻ አይደለም። ነገር ግን ጥንቃቄው እንዳለ ሆኖ ግብ ለማግባት አጥቅተን መጫወት አለብን።


© ሶከር ኢትዮጵያ

በድረ-ገጻችን ላይ የሚወጡ ጽሁፎች ምንጭ ካልተጠቀሱ በቀር የሶከር ኢትዮጵያ ናቸው፡፡ እባክዎ መረጃዎቻችንን በሚጠቀሙበት ወቅት ምንጭ መጥቀስዎን አይዘንጉ፡፡