የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት ዛሬም ሲቀጥል ቅዱስ ጊዮርጊስ ለሊጉ ዋንጫ እጅግ የተቃረበበትን ድል አስመዝግቧል፡፡ አዳማ ከተማም ሀዲያ ሆሳዕናን አሸንፎ ሁለተኛ ደረጃውን አስጠብቋል፡፡
09፡00 ላይ ሀዲያ ሆሳዕና አዳማ ከተማን አስተናግዶ 2-1 በሆነ ውጤት ተሸንፏል፡፡ ከሊጉ መውረዱን ያረጋገጠው ሀዲያ ሆሳዕና በሜዳው የሚያደርጋቸው ጨዋታዎች በገለልተኛ ሜዳ እንዲያደርግ ቅጣት የተላለፈበት በመሆኑ የዛሬው ጨዋታ ሀዋሳ ላይ ተደርጓል፡፡
የአዳማ ከተማን የድል ግቦች ታፈሰ ተስፋዬ ለእረፍት ወደ መልበሻ ክፍል ከማምራታቸው በፊት ከመረብ ሲያሳርፍ ከእረፍት መልስ ጫና ፈጥረው የተጫወቱት ሀዲያ ሆሳዕናዎች በአምራላ ደልታታተ ግብ ወደ ጨዋታው የሚመልሳቸውን ግብ ቢያስቆጥሩም የነበራቸው ብልጫ የአቻነት ግብ ለማስቆጠር በቂ አልሆነም፡፡
ድሉ አዳማ ከተማን 2ኛ ደረጃ ላይ እንዲቆይ ሲያደርገው 12ኛ እና 13ኛ ግቡን ከመረብ ያሳረፈው ታፈሰ ተስፋዬ ለ4ኛ ጊዜ የፕሪሚየር ሊጉ ከፍተኛ ግብ አግቢ ሆኖ ታሪክ ለመስራት ተቃርቧል፡፡
አዲስ አበባ ስታድየም ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን የገጠመው ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሃምራዊዎቹ ፈተና ቢገጥመውም ወደ ሊጉ ዋንጫ እጁን የዘረጋበትን ድል አስመዝግቦ ወጥቷል፡፡
አንድ ጊዜ ሞቅ አንድ ጊዜ ቀዝቀዝ ሲል የነበረው የሁለቱ ቡድኖች ፉክክር በሁለተኛው አጋማሽ ነፍዝ ዘርቶ በሁለቱም በኩል ለግብ የቀረቡ የግብ ማስቆጠር አጋጣሚዎች የተፈጠሩ ሲሆን በ72ኛው ደቂቃ ተስፋዬ አለባቸው ከርቀት አክርሮ የመታው ኳስ መረብ ላይ አርፎ ፈረሰኞቹን ለድል አብቅቷል፡፡
በጨዋታው ፊሊፕ ዳውዚ ከረዳት ዳኛው ጋር በገባው እሰጥ እገባ በቀጥታ ቀይ ካርድ ከሜዳ የተወገደ ሲሆን ከዳኛው ውሳኔ በኋላ ረዳት ዳኛውን ለመምታት ሲጋበዝ ታይቷል፡፡
ድሉ ቅዱስ ጊዮርጊስን ለሊጉ ቻምፒዮንነት እጅግ ያቃረበው ሲሆን ከዳሽን ቢራ ጋር ከሚያደርገው የ24ኛ ሳምንት ጨዋታ 1 ነጥብ ካገኘ ፐሪሚየር ሊጉ በአዲስ መልክ ከተጀመረ ወዲህ ለ13ኛ ጊዜ በአጠቃላይ ለ27ኛ ጊዜ ቻምፒዮን መሆኑን ያረጋግጣል፡፡
የደረጃ ሰንጠረዥ