ደደቢት የሲሸልሱን ኮት ዲ ኦርን በባህርዳር ብሄራዊ ስታዲየም በስዩም ተስፋዬ እና ዳዊት ፍቃዱ ግቦች ታግዞ 2ለ0 በድምር ውጤት 5ለ2 በሆነ ውጤት አሸንፏል፡፡ ስለጨዋታው የደደቢቱ ዋና አሰልጣኝ ለሶከር ኢትዮጵያ የሰጡት አስተያየት ለአንባቢያን እንዲመች አድርገን አቅርበናል፡፡
-ስለጨዋታው
በጨዋታው ስህተቶቻችንን አሻሽለናል ብዬ እገምታለው፤ ስህቶቻችንን እያስተካከልን መጥተናል፡፡ ለምሳሌ በመጨረሻ ሰዓት የሚገቡብን ግቦች ቀርተዋል፡፡ ያገኘናቸውን እድሎች አሁንም መጠቀም ወይም መጨረስ ችግር እየሆነብን ነው፡፡ ዛሬ የተሻልን ነበርን ፤ የተሻልን ስለነበርን አሸንፈናል፡፡
-ስለ አስቻለው ታመነ እና ሱሌማና አቡበክሪ
አስቻለው ጥሩ ነበር፡፡ ከምንም በላይ በረኛችን ሱሌማና መመስገን ይኖርበታል፡፡ ምክንያቱም በመጀመሪያው ግማሽ ላይ ያወጣቸው ሁለት ኳሶች ቢቆጠሩ ኖሮ ችግር ይሆንብን ነበር፡፡
-ስለ ሳምሶን ጥላሁን ጉዳት
ይህ እንግዲህ በሃኪሞች የሚታይ ነው፡፡ እኔ ሜዳ ላይ ስለነበርኩኝ ብዙም አላየሁኝም፡፡ እንግዲህ ያለውን ሁኔታ እናያለን፡፡ ተሽሎት ለሚቀጥለው ጨዋታ ይዘጋጃል ብዬ ነው የማስበው፡፡
አሰልጣኝ ዮሃንስ ሳህሌ አያይዘው ቀጣይ ተጋጣሚያቸው ጠንካራ የምዕራብ አፍረካ ብድን ስለሚሆን ጠንካራ ስራ እንደሚጠብቃቸው ጠቁመው አልፈዋል፡፡