የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከዛሬ የሴካፋ ጨዋታዎች መጠናቀቅ በኋላ አመሻሹ ላይ ልምምድ ሰርቷል፡፡ በዛሬ የልምምድ ፕሮግራም 18 ተጫዋቾች የተገኙ ሲሆን ስዩም እና ሳላዲን ሳይሰሩ ቀርተዋል፡፡
ከታንዛንያ በተደረገው ጨዋታ ያልተሰለፈው አምበሉ ስዩም ተስፋዬ በሀሙሱ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ የመድረስ እድሉ ጠባብ ሆኗል፡፡ የስዩም ጉዳት የጡንቻ መሳሳብ ሲሆን ከጉዳቱ ቢያገግምም በጨዋታው አይሰለፍም ተብሏል፡፡
ኢትዮጵያ ከ ሩዋንዳ ስትጫወት በጉልበቱ ላይ ጉዳት አስተናግዶ ተቀይሮ የወጣው ሳላዲን እስካሁን ማገገም አልቻለም፡፡ ውድድሩ እስኪጠናቀቅ ድረስ ወደ ሜዳ የመመለስ እድሉም ያበቃለት ይመስላል፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በሴካፋው ውድድር በድካም እና ጉዳት ተቸግሯል፡፡ አሰልጣኝ ዮሃንስ ሳህሌ ትላንት በሰጡት አስተያየትም 20 ተጫዋች ብቻ ማስመዝገብ በሚያስገድደው የሴካፋ ህግ ምክንያት ተጫዋቾቻቸው ለጉዳ እና ድካም እየተጋለጡ መግለፃቸው የሚታወስ ነው፡፡
የሴካፋ ግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎች ሀሙስ ሲደረጉ ኢትዮጵያ ከዩጋንዳ በ9፡30 ትፋለማለች፡፡ ከሁለቱ ጨዋቀ እስቀድሞ ደግሞ ሱዳን ከ ሩዋንዳ ይጫወታሉ፡፡