የዲኤስቲቪ እና የሊግ ኩባንያ የውል ስምምነት ይፋዊ በሆነ መንገድ ለመግለፅ ለምን ዘገየ?

በተለያዩ መንገዶች ከሚሰሙ መረጃዎች ውጭ ይፋዊ በሆነ መንገድ እስካሁን በዲኤስቲቪ እና የሊግ ኩባንያው መካከል የተደረሰው የውል ስምምነት ለምን ይፋ ሳይሆን ቀረ?  

የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አክሲዮን ማኅበር የሊጉን የቴሌቪዥን ስርጭት መብት መግዛት የሚፈልጉ ተቋማትን በግልፅ ጨረታ አወዳድሮ DStv’ም ከተወዳዳሪዎቹ የተሻለ ፋይናንሻል እና ቴክኒካል ፕሮፖዛል በማቅረብ መብቱን መግዛቱ ከተሰማ ቆይቷል። ሆኖም በተለያዩ መንገዶች ከሚወጡ መረጃዎች ውጭ የስምምነቱ ዝርዝር ነጥቦች እና ሌሎች ጉዳዮችን በተመለከተ በጋዜጣዊ መግለጫ ይፋዊ ነገሮች አልተገለፁም። በዚህም የተነሳ የተለያዩ አጠራጣሪ ነገሮች ሲነሱ ቆይተዋል። ይህን ተከትሎ ባደረግነው ማጣራት እስካሁን የዘገየበት ምክንያት አንዳንድ በቅድሚያ ሊሟሉ የሚገቡ ቅድመ ሁኔታዎችን ለማስተካከል በወሰደው ጊዜ እንደሆነና በቅርቡ ሁሉም ዝርዝር ነገሮች በይፋዊ ጋዜጣዊ መግለጫ ለስፖርት ቤተሰቡ መረጃ እንደሚሰጥ ሰምተናል። 

በሌላ ዜና ሦስቱን የትግራይ ክልል ክለቦች ዙርያ አሁን ባለው ወቅታዊ ሁኔታ አንፃር ሊጉ ለተወሰኑ ቀናት ሊራዘም ይችል ይሆን በማለት ባደረግነው ማጣራት የሊግ ኩባንያው አክሲዮን የቦርድ አመራር በቀጣይ የሚወስኑት የተለየ ነገር ከሌለ በስተቀር ውድድሩ በተባለለት ጊዜ እንደሚጀምር ሰምተናል።

©ሶከር ኢትዮጵያ