የከፍተኛ ሊግ ዕጣ የሚወጣበት ቀን ይፋ ሆኗል

የ2014 የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የዕጣ ማውጣት መርሀግብር የሚካሄደበት ቀን ይፋ ተደርጓል፡፡

በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ሥር ከሚካሄዱ ውድድሮች አንዱ የሆነው የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የ2014 የውድድር ዘመን የሚጀመርበት ቀን ኅዳር 20 መሆኑን ከቀናት በፊት በዘገባችን ጠቅሰን የነበረ ሲሆን አሁን ደግሞ ውድድሩ ከመካሄዱ በፊት ክለቦች በደንብ ዙሪያ ውይይት እንዲሁም የዕጣ አወጣጥ መርሀ-ግብር የሚካሄድበት ዕለት ኅዳር 5 እንዲሆን ፌዴሬሽኑ ለክለቦች በደብዳቤ አሳውቋል፡፡

በሦስት ምድቦች ተከፍሎ የሚከናወነው ይህ ውድድር በተጠናቀቀው የ2013 ዓመት ወርደው የነበሩ ክለቦች በወቅታዊ የሀገራችን ችግር የተነሳ የማይሳተፉ ክለቦች ካሉ ሊተኩ እንደሚችሉ የሰማን ሲሆን ፌዴሬሽኑ አያይዞ ክለቦች እስከ ጥቅምት 30 ምዝገባቸውን ማጠናቀቅ እንዳለባቸው ለክለቦች በላከው ደብዳቤ ላይ ተመላክቷል፡፡