የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ የምድብ ድልድል ይፋ ሆኗል

በቀጣዩ ሳምንት እንደሚጀምር የሚጠበቀው የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ የሁለት ምድብ ተፋላሚዎች ተለይተዋል።

በየዓመቱ ሳይቋረጥ የሚደረገው እና አስራ ሰባተኛ የውድድር ዓመቱን ያስቆጠረው የመዲናዋ ትልቁ ውድድር የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ በስምንት ክለቦችን በማሳተፍ ከመስከረም 3-15 ድረስ የሚከናወን ይሆናል። የውድድሩ የምድብ ድልድል ዕጣ ማውጣት ሥነስርዓት ዛሬ የተከናወነ ሲሆን የስፖርት ኮሚሽን በምክትል ዘርፍ የቢሮ ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ኦሜጋ ፣ የአዲስ አበባ እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝደንት ደረጄ አረጋ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመውበታል።

በኤልያና ሆቴል በተከናወነው የምድብ ድልድል ከዚህ ቀደም በሚደረገው አሰራር መሰረት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵያ ቡና በውድድሩ ላይ ካላቸው ከፍተኛ ተሳትፎ አንፃር በአንድ ምድብ እንዳይሆኑ በማድረግ የምድብ አባት እንዲሆኑ ተደርጎ የዕጣ ማውጣቱ ሥነ ስርዓት ተከናውኗል።

ምድብ ሀ

ኢትዮጵያ ቡና
ሀድያ ሆሳዕና
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
ሻሸመኔ ከተማ

ምድብ ለ

ቅዱስ ጊዮርጊስ
አዳማ ከተማ
ኢትዮጵያ መድን
መቻል

በሥነስርዓቱ ላይ ውድደሩን ለማድመቅ የተለያዩ ሥራዎች መሰራታቸው ሲገለፅ ውድድሩ የሚጀምርበት ቀን እንደ አስፈላጊነቱ ሊስተካከል እንደሚችል ተጠቁሞ ለተመልካች ክፍት መሆኑም ይፋ ተደርጓል።