ጋናዊው ተጫዋች ወደ እግርኳስ ተመልሷል

ጋናዊ አማካይ አልሀሰን ካሉሻ ከረጅም ጊዜ ጉዳት በኋላ በአንድ ዓመት ውል ወደ አዲስ ክለብ አምርቷል።

ላለፉት ዓመታት ከእግር ኳስ ርቆ የነበረው ጋናዊው የሰላሳ ዓመት የአጥቂ አማካይ አልሀሰን ካሉሻ ወደ እግር ኳስ ተመልሷል። ተጫዋቹ በ2009 ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ወደ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ፈርሞ በመጀመርያው ውድድር ዓመቱ 13 የሊግ ጎሎች አስቆጥሮ መልካም አጀማመር በማድረግ
ከክለቡ ጋር የተሳካ ዓመት ቢያሳልፍም ወደ ኢትዮጵያ ቡና ካቀና በኋላ ግን እንደተጠበቀው ሳይሆን ቀርቷል። ከቡናዎች በኋላም በመቐለ 70 እንደርታ እና ሀድያ ሆሳዕና መጫወት የቻለው ይህ አማካይ ላለፉት ዓመታት በጉዳት ምክንያት ከሜዳ ከራቀ በኋላ በአንድ ዓመት ውል የሀገሩ ክለብ ርያል ታማሌ ዮናይትድን ተቀላቅሏል።

ከዚህ ቀደም ለአራት የኢትዮጵያ ክለቦች ጨምሮ ለሀገሩ ክለቦች ታማሌ ኡትሬክት ፣ ቱራ ማጂክና ድሪምስ የተጫወተው ይህ ተጫዋች ከዓመታት በኋላ ወደ ትውልድ ከተማው ክለብ በመፈረም ወደ እግርኳስ ተመልሷል።