​የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌድሬሽን ካፍን ይቅርታ ጠይቋል

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌድሬሽን የ2018ቱን የአፍሪካ ሃገራት ቻምፒየንሺፕ (ቻን) አዘጋጅ ለመሆን ጥያቄ ያቀረበው በስህተት መሆኑን ገልጾ ለካፍ በፃፈው ደብዳቤ ይቅርታ መጠየቁን ሶከር ኢትዮጵያ ለኮንፌድሬሽኑ ቅርበት ካላቸው ታማኝ ምንጮች ማወቅ ችላለች፡፡ ፌድሬሽኑ ለካፍ የይቅርታ ደብዳቤ ቢያስገባም ለሃገር ውስጥ ሚያዲያዎች በተለይ የቻን አዘጋጅነት ጥያቄ አለማቅረቡን ሲያስተባብል ቆይቷል፡፡

ኢትዮጵያ በፌድሬሽኑ አማካኝነት የአዘጋጅነት ጥያቄ ብታቀርብም ከመንግስት የተገኘውን ድጋፍ የሚያትት ደብዳቤ ተያይዞ አለመቅረቡ ከሞሮኮ እና ኤኳቶሪያል ጊኒ ጋር ሳትፎካከር ከአዘጋጅነት ውጪ አድርጓታል፡፡ የፌድሬሽኑ ፕሬዝደንት ጁኒይዲ ባሻ ለካፍ የአዘጋጅነት ጥያቄ አለመቅረቡን ከዚህ ቀደም ለሶከር ኢትዮጵያ የሬዲዮ ፕሮግራም ቢገልፁም የካፍ የሚዲያ ኃላፊ ጁኒየር ቢኒያም በአንፃሩ ጥያቄ መቅረቡን ማረጋገጡ ይታወሳል፡፡ ይህንን ተክተሎ ነው ፌድሬሽኑ ለካፍ በስህተት ጥያቄ መቅረቡን የገለፀው፡፡

የካፍ ፕሬዝደንት አህመድ አህመድ ሰኞ ማለዳ ለሬድዮ ፍራንስ ኢንተርናሽናል (አርኤፍአይ) በሰጡት አስተያየት የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌድሬሽን የመንግስት ድጋፍ ደብዳቤ አለማካተቱ በቀላሉ ከአዘጋጅነት እጩ ለማውጣት እንደቻሉ አስረድተዋል፡፡ “የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌድሬሽን ቻንን ለማስተናገድ ፍላጎት ቢያሳይም አስፈላጊ የነበረውን የመንግስት ድጋፍ ደብዳቤ አለማቅረቡን ተከትሎ ከእጩዎች ተርታ ሰርዘናቸዋል፡፡ ” ብለዋል፡፡

ካፍ ሞሮኮን የቻን አዘጋጅ አድርጎ መምረጡን እሁድ ይፋ ያደረገ ሲሆን ሰሜን አፍሪካዊቷ ሃገር ባላት የተሟላ የመሰረተ ልማት፣ የሆቴል እና የስታዲየሞች አቅርቦት ምክንያት ከኤኳቶሪያል ጊኒ ይልቅ ለአዘጋጅነት እንድትመረጥ አስችሏታል ብለዋል ፕሬዝዳንት አህመድ፡፡

በአስተዳደራዊ ችግሮች ምክንያት መሰል ጉዳዮች በፌድሬሽኑ ላይ ሲታዩ ይህ የመጀመሪያ ግዜ አይደለም፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *