ቅዱስ ጊዮርጊስ ሦስት ወጣት ተጫዋቾቹን በውሰት ሊሰጥ ነው

ቅዱስ ጊዮርጊስ በ2010 የውድድር ዓመት ከ20 ዓመት በታች ቡድኑ ካሳደጋቸው አምስት ወጣት ተጨዋቾች መካከል ሦስቱን በውሰት ሊሰጥ ነው።

ከሦስቱ ተጨዋቾች መካከል የመስመር አጥቂው ተስፋዬ በቀለ (ቱሳ) አንዱ ሲሆን ዓምና ወደ ዋናው ቡድን ባደገበት ዓመት ብዙም የመሰለፍ እድል ባያገኝም ተቀይሮ በመግባት አጋጣሚ ተስፈኛ ተጫዋችነቱን ከማሳየቱ በተጨማሪ ለኢትዮዽያ ከ20 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ተመርጦ መጫወት ችሏል። የዘንድሮ የውድድር ዓመት ቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን ቢሾፍቱ በሚገኘው የክቡር አቶ ይድነቃቸው አካዳሚ እየሰሩ ከሚገኙት የፈረሰኞቹ ስብስብ ውስጥ ቢገኝም የተሻለ ልምድ አግኝቶ እንዲመጣ በማሰብ በአንድ ዓመት የውሰት ውል በአሰልጣኝ ደረጄ በላይ ወደሚመራው ወልቂጤ ከተማ አምርቷል ።

ሌሎች በውሰት ሊሰጡ የታሰቡት ሁለት ተጫዋቾች ማንነት ለጊዜው ያልተገለጸ ሲሆን በቅርቡ የትኛው የከፍተኛ ሊግ ቡድን ማረፊያቸው እንደሆነ የሚታወቅ ይሆናል። ያለፉትን አራት ዓመታት በዋናው ቡድን የቅድመ ውድድር ዝግጅት ወቅት ብቻ ልምምድ እየሰራ በሊግ የመጫወት እድል ያላገኘው ግብ ጠባቂው ባህሩ ዘንድሮ ለቡድኑ ሦስተኛ ግብጠባቂ ሆኖ እንዲያገለግል ፊርማውን ማኖሩ ይታወቃል።

ከሚሌንየሙ በፊት በርካታ ተጫዋቾችን ከተስፋ ቡድኑ በማሳደግ ይጠቀስ የነበረው ቅዱስ ጊዮርጊስ በሚሌንየሙ መጀመርያ በአሰልጣኝ ስሬዮቪች ሚሉቲን እየተመራ ከ6 በላይ ተጫዋቾችን በአንድ ጊዜ በማሳደግ የመጀመርያ ተሰላፊ እስከማድረግ ደርሶ ነበር፡፡ ሆኖም በሒደት ወደዋናው ቡድን ለሚያድጉ ተጫዋቾች የሚሰጠው ድል እየተመናመነ መጥቷል፡፡