የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት 4 ጨዋታዎች ዛሬ ሲደረጉ በጉጉት የተጠበቀው የሸገር ደርቢ ካለግብ ተጠናቋል፡፡ ድሬዳዋ ከተማ እና አዳማ ከተማ አሸንፈዋል፡፡ የደቡብ ደርቢም ካለ ግብ ተጠናቋል፡፡
ወደ ሆሳዕና የተጓዘው ድሬዳዋ ከተማ 2-0 አሸንፎ ደረጃውን አሻሽሏል፡፡ የብርቱካናማዎቹን የድል ግቦች በላይ አባይነህ በ18ኛው እንዲሁም ፉአድ ኢብራሂም በ60ኛው ደቂቃ አስቆጥረዋል፡፡ በቅርቡ ወደ ድሬዳዋ ከተማ የተዛወረው ፉአድ በሊጉ የመጀመርያ ግቡን ከመረብ አሳርፏል፡፡ በጨዋታው ላይ የሀዲያ ሆሳዕናው ተመስገን ገ/ፃዲቅ ያገኘውን የፍፁም ቅጣት ምት አምክኗል፡፡
አዳማ ላይ አዳማ ከተማ አርባምንጭ ከተማን አስተናግዶ 1-0 በማሸነፍ ወደ ሁለተኛ ደረጃ ተመልሷል፡፡ አዳማ ከተማን የድል ግብ ከመረብ ያሳረፈው ታፈሰ ተስፋዬ ነው፡፡ ታፈሰ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ግቦች 11 በማድረስ የሊጉን ከፍተኛ ግብ አግቢነት መምራቱን ቀጥሏል፡፡
ወላይታ ድቻ በአቻ ውጤቱ ቀጥሏል፡፡ ቦዲቲ ላይ ሲዳማ ቡናን ያስተናገደው ወላይታ ድቻ ካለ ግብ አቻ ተለያቷል፡፡ ይህ ውጤት ለድቻ በተከታታይ 4ኛ ካለግብ አቻ የወጣበት ጨዋታ ሆኗል፡፡
በጉጉት የተጠበቀው የሸገር ደርቢ ለተካታታይ ጊዜ ካለግብ ተጠናቋል፡፡ በከፍተኛ ድባብ እና በተመልካች በተሞላ ሜዳ ላይ ጨዋታቸውን ያደረጉት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኢትዮጵየ ቡና እንደአንደኛው ዙር ሁሉ ካለግብ ተጠናቋል፡፡
በጨዋታው የመጀመርያ ደቂቃዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ በአዳነ ግርማ እና ሳላዲን ሰኢድ አማካኝነት የግብ ሙከራዎችን ሲያደርግ ኢትዮጵያ ቡናዎች በሁለተኛው አጋማሽ በእንቅስቃሴ የወሰዱትን የበላይነት ወደ ግብ እድልነት መቀየር ሳይችሉ ቀርቷል፡፡
የደረጃ ሰንጠረዥ
የሊጉ 18ኛ ሳምንት የመጨረሻ ሁለት ጨዋታዎች ነገ ሲደረጉ በ09፡00 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ ሀዋሳ ከተማ ይጫወታሉ፡፡ 11፡30 ላይ መከላከያ ዳሽን ቢራን ያስተናግዳል፡፡